Netsanet: Februar 2016

Dienstag, 23. Februar 2016

ገራፊዬን አየኹት ፡ (አቤል ዋበላ

ገራፊዬን አየኹት ፡ (አቤል ዋበላ)
.


ቀልድ ያለፈበት ጨዋታ ሆኗል፡፡ አሁን ዘውጉ ተቀይሯል፡፡ ፍጥጥ ግጥጥ ያለ ዕውናዊ ድርሰትን መመልከት ይዘናል፡፡አይን አያየው የለም፡፡ አሁን ደግሞ ገራፊዬን አሳየኝ፡፡ በኮምፒዩተር የኤሌክትሪክ ገመድ ጀርባዬ እስኪቀደድ የገረፈኝን፣ በመጥረጊያ እንጨት ውስጥ እግሬን ያነደደኝን፣ እጄ በካቴና ታስሮ ወለል ላይ ያንከባለለኝን፣ ጨለማ ቤት ውስጥ አስገብቶ ከየት እንደመጣ በማላውቀው ጅራፍ አሳሬን ያበላኝን፣ እናቴን ከመቃብር ጠርቼ “አንቺ እናቴ ለምን ጥሩ ሁን ብለሽ አሳደግሽኝ? ብዙ ክፉ ሰዎች እንዳሉ ለምን አልመከርሽኝም?” ብዬ እንድወቅሳት ያደረገኝን፣ ወንድ፣ የወንዶች ቁና በካቴና የታሰረን ሰው በዕኩለ ሌሊት ጠርቶ አፉ ውስጥ ጨርቅ ወትፎ የሚደበድብ በአይኔ በብረቱ አየኹት፡፡

ዮናታን ተስፋዬ ለጊዜያዊ ቀነ ቀጠሮ አራዳ ፍርድ ቤት እንደሚቀርብ ሰምቼ ነው ወደዚያ የሄድኩት፡፡ ይህችን የተለመደች ሰርከስ ሁሉም የፖለቲካ እስረኛ ይወዛወዛታል፡፡በማዕከላዊ ይጀመራል ከዚያ አራዳ ፍርድ ቤት ይቀጥላል፡፡ የማዕከላዊ ደብዳቢዎች በጨለማ የሚያሰቃዩትን እስረኛ በቀን ሰው መስለው (ወገኞች ናቸው አንዳንዴማ ዩኒፎርምም ያጠልቃሉ) ፍርድ ቤት ያቀርቡታል፡፡ ውሸት ውሸቱን ይቀባጥራሉ፡፡ “ግበረ አበሮቹን በኢንተርፖል እያሳደድን ነው፣ ክቡር ዳኛ በዋስ ከተለለቀቁ ልማታችንን ያደናቅፋሉ፡፡ ወህኒ ሰብረው እስረኛ ያስፈታሉ” የመሳሰሉትን በጠራራ ጸሐይ ይቀባጥራሉ፡፡ እየቀለድኩኝ አይደልም የምሬን ነው እንዲህ አይነት በሬ ወለደ ምክንያት በጆሮዬ ሰምቻለው፡፡ ዳኛውም አብሮ ይተውናል፡፡ የፈለጉትን ቀን ያህል ያራዝማል፡፡

ገራፊዬንም ያየሁት እኔንና ጓደኞቼን እንደነዳው እንዲሁ ተረኛውን ገፈት ቀማሽ ሲያመጣ ነው፡፡ ላንዳፍታ አይኖቻችን ተጋጩ፡፡ አስተውሎኝ ይሁን አይሁን አላውቅም በፍርድ ቤቱ ቢሮዎች መሐል ገብቶ ተሰወረ፡፡ እኔ ግን በእርግጠኝነት ለይቸዋለው፡፡ ውስጤ ዳግም ተቆጣ፡፡ እስር ቤት ብቻዬን ደጋግሜ ባሰብኩት ቁጥር እንደአዲስ የልቤ ቁስል ያመረቅዝ ነበር፡፡ ቂም ስቋጥር እና ስፈታ ከአመት በላይ ቆይቻለው፡፡ ቂም ይዣለው በውድም ሆነ በግድ ኢትዮጵያዊ በሆነ ሁሉ ላይ ቂም ይዣለው፡፡ እንዴት ሰው በሀገሩ ይህንን ጉድ ተሸክሞ ይኖራል? እንዴት እንደዚህ አይነት ተቋም በመዲናይቱ እምብርት ላይ አስቀምጦ ዝም ይላል? ይህን ባርቤሪዝም ጌጡ ካደረገ ማኀበረሰብ ጋር በቀላሉ የማይበርድ ግጭት ውስጥ ነኝ፡፡ ስለዚህ በመንገድ ስታገኙኝ ፊቴ ጥቁር ብሎ ብታገኙኝ “ምን ሆነህ ነው?” አትበሉኝ፡፡ ቂም ይዤ ነው፡፡ ተራ ማኩረፍ አድርጋችኹ አትውሰዱት ስር የሰደደ ከነፍስ የሚቀዳ ጸብ ነው፡፡

በግርፋት የተሰነጠቀውን ጀርባዬ በቅባት ላሹኝ ዕድሜ ለእነ ኤባ ቁስሉ እዛው ማዕከላዊ ነው የዳነው፡፡ የልቤ ስንጥቅ ግን አልዳነም ፡፡ ያ ዘላለም ክብረት “ምድር ብዙ ክፋት የሚፈጸምባት ቦታ ናት በእኛ ላይ የደረሰውም አዲስ ነገር አይደለም” እያለ ብዙ እንዳላዝን ቢመክረኝም ያቄመው ልቤን ሊያሸንፈው አልቻለም ነበር፡፡ የተገኘሁበት፣ ያሳደገኝ ማኀበረሰብ ላይ እንዳቄምኩኝ ከእስር ወጣኹኝ፡፡ ባለፉት አራት ወራት በአንጻራዊ ነጻነት ማሳለፌ ግን ትንሽ እንዳዘናጋኝ የገባኝ ግን በቀደም ገራፊዬን ያየኹት ቀን ነው፡፡ወይ ጊዜ ስንቱን ያስረሳል አልኩኝ፡፡ አሁን ከእስር መፈታት ብርቅ የሆነበት ጊዜ አልፏል፡፡ ቁስሌ ዳግም አመርቅዟል፡፡ ገራፊዬን እና አለቆቹን የያዘው ህንጻ ካልፈረሰ አልያም ሙዚየም ካልሆነ ዕርቅ የማይታሰብ ነው፡፡ ድሮ እስር ቤት ሳለኹኝ በእስረኛ ማጓጓዣ መኪና ወደ ፍርድ ቤት ስንመላለስ በመስኮት ስመለከተው የዕለት ጉርሱን ለማብሰል የሚራኮተው አዳሜ አሁንም ውስጡ ሁኜ ስመለከተው ከሆዱ በቀር የኔ ቁስል ግድ የሰጠው አይመስልም፡፡ ስለዚህ ምን አዲስ ነገር ተፈጠረ ብዬ ይቅር እላለው? ውስጤ የበለጠ ስለሻከረ እምቢኝ ብያለው፡፡ ይህ የአንዲት ነጠላ ነፍስ መብት ነው፡፡ በገዛ ነፍሴ ጥላቻን ማርገዝ መብቴ ነው፡፡ ከፈለጋችኹ ለዐቃቤ ሕግ ንገሩትና በፊት ‘የማኀበረሰቡን ጤና እና ደህንነት ለአደጋ በማጋለጥ’ እንደ ከሰሰኝ አሁን ደግም ‘በማኀበረሰቡ ላይ ስር የሰደደ ጥላቻና ቂም በመቋጠር’ ይክሰሰኝ፡፡

እነ ኤቢሳ አካላዊ ቁስሌን እንደሳምራዊው ሰው በቅባት እንዳሹልኝ አሁን ደግሞ ዘመዶቻቸው የተሰበረ መንፈሴን የቆሰለ እኔነቴን ሊጥገኑ ተነስተዋል፡፡ የእነኤቢሳ፣ የእነቶፊቅ እና የእነ ቶላ ዘመዶች እኔን ከህመሜ ሊያድኑኝ ደማቸውን እየከፈሉ መሆናቸውን ድፍን ፌስቡክ እየተመለከተው ነው፡፡ አዲስ አበቤ “አገር ሊያፈርሱ ነው ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር አትኖርም” ቅብርጥሴ ቅብርጥሴ ቢልም እኔ ግን ከሚፈርሰው አገር ከፒያሳ ከፍ ብሎ ያለው ማዕከላዊ ጎልቶ ይታየኛል፡፡ ስለዚህ በመሬት ላይ ዋጋ እየከፈሉ ያሉትን ወገኖቼን ይቅር ብያለው፡፡ ከነዚህ በቀር ሌላው ማኀበረሰብ “እርሱ” አይደለም “እኔ” ራሱ ይቅርታን አያገኛትም፡፡ አራዳ ፍርድ ቤት መሄዴ አይቀርም፡፡ በማዕከላዊ በርም አልፋለው፡፡ በየጊዜው እየሄደኩኝ ከገራፊዎቼ አንዱን እያየው ጥላቻዬን እያደስኩኝ እመጣለው፡፡ ቁስሉ ይበልጥ እንዲቆጠቁጠኝ ወደገራፊዬ ተጠግቼ አይኖቹን በአይኖቼ አድናለው፡፡ አይገርምም ግን ………….…ገራፊዬ እስካሁን እዚያው ነው፡፡
http://wp.me/p5L3EG-aw

Sonntag, 14. Februar 2016

የጋማ ከብቶች” – ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

“የጋማ ከብቶች” – ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

ያንተ ታሪክ፣ ባህል፣ ማንነትና ቅርስ ስለሆነ ብቻ ዝም ብለህ አትዋጠው፤ አንጥረው፡
፡ ዕውቀት ወደሚባል፣ ማስረጃ ወደሚባል፣ መረጃ ወደሚባል፣ ክርክር ወደሚባል፣
ተጠየቅ ወደሚባል፣ ኅሊና ወደሚባል እሳት ላይ አውጣው፡፡ ይነጥራል፡፡

   በቀደም ድሬዳዋ ላይ ዓሣ ዘነበ ብለን ከአንድ ወዳጄ ጋር ስናወራ፤“ባክህ ይሄ እንኳን የጋማ ከብቶች ወሬ ነው” አለኝ፡፡ እኔም አነጋገሩ ገርሞኝ፤“የጋማ ከብቶች ደግሞ እነማን ናቸው” ስል ጠየቅኩት፡፡

“የማያመነዥኩ ናቸዋ” አለና አሳጠረው፡፡
“እኮ ከድሬዳዋ ዓሣ ጋር ምን ያገናኘዋል?”

እኔ ድሬዳዋ እንኳን ዓሣ፣ የዓሣ ፋብሪካ ቢወርድላት ችግር የለብኝም፡፡ ለምን፣ እንዴት፣ መቼ፣ ማን፣ ፊትና ኋላ፣ ቀኝና ግራ የሚባሉ ነገሮች ፋሽናቸው አለፈ እንዴ? አንድ ሚዲያ፤ ‹ዓሣ ዘነበ› ከማለቱ በፊት በጋዜጠኛውና በሚዲያ ኃላፊዎች ላይ ‹ማመዛዘን› የሚባለው ነገር መዝነብ ነበረበት፡፡ ያንን የዘገበ ዘጋቢ ዓሣ ሊያዘንብ የሚችል ታሪካዊ፣ ሳይንሳዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ አየር ንብረታዊ፣ ሌላም ምክንያት መኖር አለመኖሩን ሳያጣራ፣ በየቦታው ተዘዋውሮ ሳያረጋግጥ፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ በኅሊናው መዝኖ ከግምት በላይ ሳያልፍ፣ እንዴት ለዘገባ ያበቃዋል፡፡ ይኼ የጋማ ከብትነት ይባላል፡፡

የጋማ ከብት ይበላል ግን አያመነዥክም፡፡ ያገኘውን መዋጥ ብቻ ነው፡፡ እስኪ የቀንድ ከብቶችን ተመልከት፤ቀን የበሉትን ማታ ጋደም ብለው በጽሞና ሲያመነዥኩት ታዳምጣለህ፡፡ ይፈጩታል፣ ይሰልቁታል፣ ያጣጥሙታል፣ ያወጡታል፣ ያወርዱታል፡፡ አንዴ ገባ ብለው እንዲሁ አይተውትም፡፡ ፊውዝ እንኳን የማይስማማው የኤሌክትሪክ ኃይል ሲመጣ አላሳልፍም ብሎ ራሱ ይቃጠላል፡፡ ብሬከር እንኳን በዐቅሙ የማይሆን ኤሌክትሪክ ሲመጣ ይዘጋል፡፡ እንዴት ሰው እንደ ጋማ ከብት የሰጡትን ሁሉ ይውጣል፡፡  

አሁን በየስብሰባውና በየሚዲያው ‹የመለስ ራእይ› ሲባል እንሰማለን፡፡ የመለስ ራእይ ምን እንደሆነ አንድ፣ ሁለት፣ ሦስት ብለህ ግለጠው ቢባል ስንቱ ያውቀዋል? የሆነ ቦታ ሲባል ስለሰማ ሳያመነዥክ እርሱም ይለዋል እንጂ፤ እውነት ይሄ ሁሉ ሰው ራእዩን ዐውቆት፣ ከዚያ ገብቶት፣ ከዚያም ተስማምቶበት ነው እያወራ ያለው?

 አንዱ፣ እገሌ የተባሉት ባለሥልጣን፣ ሥራ የሚቀጥሩት በዘመድ ነው ሲባል ይሰማል፡፡ ጓደኞቹ ደግሞ ‹የአንተ አገር ሰው’ኮ ናቸው› ይሉታል፡፡ ይሄ ነገር ሲደጋገምበት ‹ለምን አልጠይቃቸውም› ብሎ ቢሯቸው ሄደ፡፡ ምናለ ቢያንስ – የት ሀገር፣ የት ቀበሌ፣ የት መንደር ናቸው የሚለውን እንኳን ቢያጣራ፡፡ ቢሯቸው ገብቶ የሀገራቸው ሰው መሆኑን ይገልጥና ሥራ ይለምናል፡፡ እርሳቸውም በመንደርና በጎጥ የጠበቡ ነበሩና፤ ‹ለመሆኑ ሀገርህ የት ነው?› ይሉታል ‹ከእርስዎ ሀገር› ይላል፡፡ ‹የኔ ሀገር የት ነው?› ሲሉት ‹ከኛ ሀገር› አለ አሉ፡፡

አሁንማ የጋማ ከብቶች ወረሩን’ኮ፡፡ ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው፣ ማኅበራዊ ሚዲያው፣ ሥልጣኑ፣ ኪነ ጥበቡ፣ ቤተ እምነቱ፣ ምሁርነቱ፣ ንግዱ፣ ፓርቲው፣ ምኑ ቅጡ– በጋማ ከብቶች እየተሞላ ነው፡፡ እስኪ ከፈለግህ ‹እገሌ ሞተ› በልና ፌስ ቡክ ላይ ለጥፍ፡፡ ምንም ነገር ሳያጣራ ግማሹ ፕሮፋይል ፒክቸሩን ጥቁር ያደርጋል፣ ሌላው ‹አር. አይ. ፒ› ይላል፣ ሌላው ደግሞ ምናልባት ልቅሶ ተቀምጦ የዕድር ብር በልቶ ይሆናል፡፡ ‹በዓሉ ግርማ ዳጋ እስጢፋኖስ ተገኘ› ሲባል በአንድ ጀልባ ሮጦ ሊያጣራ የሚችለው የባሕር ዳር ነዋሪ፣ አብሮ ‹ሼር› እና ‹ላይክ› ካደረገ ከዚህ በላይ የጋማ ከብትነት ምን አለ?

ወዳጄ፣ማመን ማለት ፈጽሞ አእምሮን መነሣት አይደለም፡፡ አእምሮ የፈጠረልህን ፈጣሪ ከሆነ የምታምነው ማመዛዘንን እምነት አይቀማህም፡፡ የቅዱስ እስጢፋኖስን በዓል አከብራለሁ ብሎ የሄደ ምእመን፤‹ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ ተወገረ› ሲሉት ‹እልልልልልል› ብሎ የሚያቀልጠው ከሆነ፣ ዐጸዱ በጋማ ከብቶች ተሞልቷል ማለት ነው፡፡ እንዲህ ያለው የጋማ ከብትነት ነው ፓስተሮቻችንና አስተማሪዎቻችን ልብሳችሁን አውልቁ፣ ሣር ብሉ፣ መሬት እንዳይነካን አጎንብሱና እንቁምባችሁ ሲሉን ያለማመንዠክ እንድንቀበላቸው ያደረገን፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን እናቱ ትምህርት ቤት ባስገባቺው ጊዜ፣መምህሩ የእብራይስጥን ፊደል ሲያስቆጥረው፤ ‹አሌፍ› በል አለው፡፡ ‹አሌፍ› አለ፡፡ ቀጥሎ ደግሞ ‹ቤት› በል አለው፡፡ ዝም አለ፡፡ መምህሩ ተናደደና፤ ‹ለምን ቤት አትልም?› ሲል ተቆጣው፡፡ ሕጻኑ ክርስቶስም፤ ‹መጀመሪያ የአሌፍን ትርጉም ንገረኝና ከዚያ ቀጥዬ ቤት እላለሁ› አለው ይላል ተአምረ ኢየሱስ፡፡ ታዲያ ምነው የእርሱ ተከታዮች መጠየቅንና መመዘንን ፈሩ? ለምንስ የጋማ ከብትነት በዛ?

በደርግ ዘመን፤ ‹ጓድ መንግሥቱ እንዳሉት› እየተባሉ የሚነገሩት ጥቅሶች ሁሉ ብዙዎቹ መንግሥቱ ኃይለማርያም ራሳቸው የማያውቋቸው እንደሆኑ በኋላ ታውቋል፡፡ እንዲያውም በአንድ ስብሰባ ላይ ‹ሰውን ሰው ያደረገው ሥራ ነው› ብለዋል ጓድ መንግሥቱ ብሎ አንዱ ካድሬ ይጠቅሳል፡፡ ያውም ራሳቸው መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ባሉበት፡፡ እርሳቸው ራሳቸው ገርሟቸው፤ ‹ኧረ ይሄን ነገር እኔ አልተናገርኩም› ይሉና ከስብሰባው በኋላ ያስጠሩታል፡፡ ‹ይህ ንግግር የኔ መሆኑን ከየት አገኘኸው?› ሲሉት ‹መቼም እንዲህ ያለ ንግግር ከእርስዎ አፍ ካልሆነ በቀር ከአድኃሪያን አፍ አይወጣም ብዬ ነው› አለ አሉ፡፡ ካድሬ ምን አለበት፤ ‹ነው› ከተባለ ነው፣ ‹አይደለም› ከተባለ፣ አይደለም ብሎ ይኖራል፡፡

በወዲህም ሆነ በወዲያ ቆመው ሚዲያውን የተቆጣጠሩት ወገኖቻችን ጥቂት ማመንዠክ ቢችሉ ኖሮ እኛን የአህያ ሆድ አድርገው አይቆጥሩንም ነበር፡፡ የሚበሉት እህል ይለያያል እንጂ ሁለቱም አያመነዥኩም፡፡ ሁለቱም ወዳጆቻቸው የነገሯቸውን ሳያመሰኩ ይውጣሉ፤ ሁለቱም ጠላት ከሚሏቸው የሚመጣውን አይቀበሉም፡፡ እነርሱን እስከ ደገፈና ጠላቶቻቸውን እስከ ተቃወመ ድረስ ሁለቱም ማንጠሪያ የላቸውም፡፡

በተለይ ደግሞ ዘረኝነትና ማይምነት ሲጨመሩበት፣የጋማ ከብትነት የከፋ ይሆናል፡፡ ዘረኞች ከራሳቸው ወገን የሚመጣውን ሁሉ እንዳለ ይውጡታል፡፡ ከዚያ ውጭ ያለው ሁሉ ሊያጠፋቸው፣ ሊቀማቸው፣ ሊያንቋሽሻቸው የሚመጣ አድርገው ስለሚመለከቱት ከወገናቸው ውጭ ማንንም አያምኑም፡፡ በባለሞያ ያልተቃኙ፣ በገለልተኝነት ያልተበየኑ፣ በማስረጃ የማይበጠሩ፣ ስሜትና እውነትን ያልለዩ፣ የታሪክ ድርሳናት በየቦታው ሲታተሙና ‹ለብሔረሰቡ› ሲሠራጩ ሃይ ባይ የላቸውም፡፡ ዘረኞች እውነትን በዘር መነጽር ነው የሚያዩዋት፡፡ ምን ተነገረ? ሳይሆን ማን ተናገረ? ነው ቁም ነገሩ? ቀጥሎ ደግሞ የኛ ወገን ነው ወይስ የነዚያ? ይባላል፡፡ የራስህ ወገን የነገረህን ዝም ብለህ መጋት ነው፡፡ ቢቻል ቢቻል ጀግና ነህ፣ ማራኪ ነህ፣ የሠለጠንክ ነህ፣ የዚህና የዚያ ምንጭ ነህ፣ ድንቅ ባህልና ምርጥ ታሪክ አለህ ይበልህ፡፡ ሳታመነዥክ ትጋተዋለህ፡፡ ይኼ ካልሆነ ደግሞ ተጨቁነህ፣ ተረግጠህ፣ ማንነትህ ተረስቶ፣ ከሰው በታች ሆነህ ነበር፤ እነ እገሌና እነ እገሊት ጠላቶችህ ናቸው ብሎ ሙሾ ያውርድልህ አሁንም ትጋተዋለህ፡፡ ማንጠር የሚባል ነገር የለም፡፡

ዘረኝነት ማንጠር የሚባለውን ሞያ አጥፍቶብናል፡፡ ቅቤን ከአንጉላው የሚለየው ማንጠር ነው፡፡ ሲነጠር ቅቤው ለብቻው፣ አንጉላው ለብቻው ተለይቶ ቁጭ ይላል፡፡ ለአንጉላ ተብሎ ቅቤ አይጣልም፤ ለቅቤም ተብሎ አንጉላ አይበላም፡፡ ይነጠራል እንጂ፡፡ ያንተ ታሪክ፣ ባህል፣ ማንነትና ቅርስ ስለሆነ ብቻ ዝም ብለህ አትዋጠው፤ አንጥረው፡፡ ዕውቀት ወደሚባል፣ ማስረጃ ወደሚባል፣ መረጃ ወደሚባል፣ ክርክር ወደሚባል፣ ተጠየቅ ወደሚባል፣ ኅሊና ወደሚባል፣ እሳት ላይ አውጣው፡፡ ይነጥራል፡፡ አንጉላው ከቅቤው ይለያል፡፡ ካልሆነ ግን በተለይ የማያመነዥኩ ሰዎች ሆድ ውስጥ ከገባ አደጋ ነው፡፡

እንክርዳድ እክርደድ የተንከረደደ

ስንዴ መስሎ ገብቶ ስንቱን አሳበደ፤ የተባለው ለዚህ አይደል፡፡

ማይምነትን በእናቶቻችን ቋንቋ ለመተርጎም ‹የማይለቅም፣ የማያነፍስ፣ የማያበጥር፣ የማይነፋ፤ እንዲሁ የሚያስፈጭና የሚበላ› ማለት ነው፡፡ እናቶቻችን እህሉን ከቆሻሻው ለመለየት የቻሉትን በእጅ ይለቅማሉ፣ ያልተቻለውን በሰፌድ ያነፍሳሉ፣ የተረፈውን በማበጠሪያ ወንፊት ያበጥራሉ፡፡ ተፈጭቶ ከመጣ በኋላ ደግሞ በጥቅጥቅ ወንፊት ይነፉታል፡፡ ይኼ ሁሉ ልፋት ዓይነተኛውን እህል ለማግኘት ነው፡፡ ዓይነተኛውን እውነት ለማግኘትም በመረጃና በማስረጃ፣ በዕውቀትና በብስለት፣ በተጠየቅና በመጠንቀቅ መልቀም፣ ማንፈስ፣ ማበጠርና መንፋት ያስፈልጋል፡፡ 
ምሁራኑ እንኳን በየዐውደ ጥናቱ፣ ጥናታዊ ጽሑፍ ብለው የሚያቀርቡት ተዘጋጅቶና ተሰናድቶ የመጣውን ‹ዳታ›፣ ለበዓሉ የሚስማማውን ቀለም፣አየሩና ነፋሱ ሲለው የከረመውን እንጂ ዘወር ያለ፣ የተመዘነ፣የነጠረና፣የተመረመረ ነገር አይናገሩም፡፡ በዜና የሰማነውን በጥናታዊ ጽሑፍ ቅርጽ ያቀርቡታል፡፡ ሳያመነዥኩ ያቀርባሉ፤ ሳናመነዥክ እንበላለን፡፡

በድሬዳዋ የተጀመረውን ነገር ድሬዳዋ ላይ በተፈጸመ የጋማ ከብትነት እንዝጋው፡፡ መምህሩ ውጭ ቁጭ ብሎ ተማሪውን ይጠራውና፤ ‹እዚያ ክፍል ሄደህ እኔ መኖሬንና አለመኖሬን አይተህ ንገረኝ› ይለዋል፡፡ ተማሪውም ቀጥ ብሎ ሄዶ በመስኮት ያይና ተመልሶ መጥቶ ‹የሉም› ይለዋል፡፡ ይሄኔ መምህሩ በጥፊ ተማሪውን መታው፡፡ ተማሪው የደረሰበትን ይናገርና አባቱን ይዞት ይመጣል፡፡ አባትዬውም እንደመጡ፤ ‹እንዴት ልጄን ትመታለህ!› ብለው ይፎክራሉ፡፡ መምህሩም፤ ‹ታዲያ ለምን ከክፍል ውስጥ የለም ይለኛል› አላቸው፡፡ አባት መለስ ይሉና ልጃቸውን፤ ‹እንደዚህ ብለሃል› ይሉታል፡፡ ‹አዎ› ይላል ተማሪው፡፡ ‹መምህሩን ከክፍል ውስጥ የሉም አልክ› አባት አጽንተው ጠየቁ፡፡ ‹አዎ ብያለሁ› ይላል ልጅ፡፡ አባትም ተናድደው፤ ‹ታድያ እርሳቸው ከሌሉ ማን እያስተማረህ ነው ተምሬ መጣሁ የምትለው› ብለው ልጃቸውን ጥፊ ደገሙት ይባላል፡፡ እንዲህ ነው የጋማ ከብትነት የመጣልህን መዋጥ፡፡

http://wp.me/p5L3EG-an

Freitag, 12. Februar 2016

” ዲሞክራሲ -101″…”መካሪ አያሳጣህ!” ተጳፈ ለሀይሌ ገ/ስላሴ በኤርምያስ ለገሰ

” ዲሞክራሲ -101″…”መካሪ አያሳጣህ!”
ተጳፈ ለሀይሌ ገ/ስላሴ
በኤርምያስ ለገሰ12743851_1068360716554981_1821910993132103980_n
ይቺን አጭር ፅሁፍ ለመጫር የገፋፋኝ በዛሬው እለት አትሌት ሐይሌ ለአንድ የውጭ ሚዲያ የሰጠውን አስተያየት በማዳመጤ ምክንያት ነው። አላማዬ ሐይሌ የተናገረውን ሁሉ ለመቃወም አይደለም። ወይም አንዳንድ ” ልወደድ ባይ ደካማ” ሰዎች እንደሚያስቡት አትሌቱ የተጐናፀፈውን ዝና ለማጉደፍ አስቤ አይደለም።
ለእኔም ሆነ ለመላው ኢትዬጲያውያን ሐይሌ በአለም አቀፍ መድረክ ኢትዮጵያዊ አርማችን ነው። አርማን ማቆሸሽ ደግሞ ሐገርን ከመክዳት የሚተናነስ አይደለም። ሀይሌ የማይቻል የሚመስል ነገርን በአለም አቀፍ መድረክ እንደሚቻል ያሳየልን በአርአያነት የምናወድሰው ብሔራዊ ሃብታችን ነው። ሐይሌ ሃይላችን ነው። በስደት አለም እንኳን አንዳንድ ሰዎች ሀገራችንን ጠይቀውን ማወቅ ከተሳናቸው ለማስረዳት ከምናነሳቸው ብርቅዬ ስሞች አንዱ ሐይሌ ገ/ሥላሴ የሚለውን ነው።
ይሔ ማለት ግን አትሌት ሐይሌ ተራራ የሚያካክሉ ስህተቶችን እየሰራ እያየን እና እያዳመጥን ዝምታን እንመርጣለን ማለት አይደለም። አንፃራዊ ትምህርት እና ንቃት የሚጠይቅ ቦታ ላይ እየገባ ” አላዋቂ ሳሚ” ሲሆን በአርምሞ አንመለከተውም ።…አካፋን አካፋ ማለት ይኖርብናል ። አስተውሎ ለተመለከተው የሀይሌ መውረድ የእኛም መውረድ ነው፣…የሀይሌ አልቦነት የእኛም አልቦነት ነው፣… የሀይሌ መካሪ ማጣት ሀገሪቷ አዋቂ ሽማግሌ የላትም ወይ የሚያስብል ነው። እንደዚህ አይነት ግድፈቶች በእንጭጩ ካልተስተካከሉ ደግሞ ውርደቱ ከግለሰብ ተሻግሮ አገራዊ ይሆናል። አይበለውና አትሌቱ አሁን የሰጠውን አስተያየት “የአውሮፓ ህብረት” ስብሰባ ላይ በእንግድነት ተገኝቶ ቢናገረው ምን ይውጠን ነበር?…በማርቲን ሉተር ኪንግ ግዛት የሆነችው አትላንታ ተገኝቶ የደሰኮራት ቢሆን ምን ያህል ያሸማቅቀን ነበር?…
( ወግን ወግ አነሳውና አንድ ነገር ትዝ አለኝ ። ወጉን ያጫወቱኝ በአትላንታ የሚኖሩ ኢትዬጲያውያን ናቸው። በተመሳሳይ መንገድ እንደራሴ የማምነው የኢሳት ባልደረባም በቦታው በአካል ተገኝቶ ስለነበር ይህንኑ አውገቶኛል።
እንዲህ ነበር የሆነው፣
በአትላንታ የሚኖሩ ኢትዬጲያውያን ክብር ለሚገባው ክብር ለመስጠት ሰፊ ፕሮግራም ያዘጋጃሉ። ከእነዚህ ታላቅ ኢትዬጲያውያን መካከል አትሌት ሐይሌ ገ/ሥላሴ ይገኝበታል። ፕሮግራሙ ሲጀመር ከነሙሉ ክብሩ ወደ መድረክ የተጠራው አትሌት ሐይሌ ሙቀቱ በፈጠረለት ወኔ ተነሳስቶ ታሪካዊ ንግግር አደረገ። ንግግሩ በከፍተኛ ጭብጨባ በመታጀቡ ሐይሌ ማቆም አልቻለም። በማሳረጊያውም በረጅሙ ተንፍሶ ” ኢትዬጲያ ብሆን ይሔን አልናገርም ነበር፣ የሚደርስብኝን ስለማውቅ !” በማለት ሀገሪቱ ያለችበትን ሁኔታ ለሕዝቡ በቁጭት አስረዳ ።በድጋሚ ከአዳራሹ የተሰማው ጭብጨባ፣ ፊሽካና ሳቅ ከአትላንታ ተነስቶ፣ አትላንቲክን አቋርጦ የሚኒሊክ ቤተመንግሥት ተሰማ።)
ወደቀደመው ጉዳያችን ስንመለስ አትሌት ሐይሌ በተደጋጋሚ ጊዜ የሚፎርሸው በምን ምክንያት ነው?… የሚናገረውን ነገር በጥልቀት ያውቀዋል ወይ?…ከጀርባ ሌሎች ምክንያቶች ይኖሩት ይሆን?…ወዘተ የሚሉትን ጥያቄዎች ማቅረብ ተገቢ ይሆናል። በእኔ እምነት አምስት መሰረታዊ ምክንያቶች ያሉ ይመስለኛል፣
1• ” የእውነተኛ ዲሞክራሲን” ትርጉም ያለማወቅ
2• የኢትዮጵያ ችግሮች ሁሉ ማጠንጠኛ ” የእውነተኛ ዲሞክራሲ እጦት” መሆኑን ያለመገንዘብ
3• “ፓለቲካ ሳይንስም ጥበብም” መሆኑን ያለማወቅ
4• ለከት የለሽ የሀብት ማሰባሰብ ፍላጐት እና
5• አገዛዙ የደረሰበት ( በድብቅ ሳያውቅ ያስፈፀመው) ከባድ ወንጀል መኖር
ለዚህ አጭር ማስታወሻ በመጀመሪያዎቹ ሶስት ነጥቦች ላይ ትዝብቴን ማስፈር እፈልጋለሁ ።
1• “የእውነተኛ ዲሞክራሲን” ትርጉም ያለማወቅ
እንኳን ለሀይሌ የተለያዩ የፓለቲካል ኢኮኖሚ መጵሀፍቶችን ላገላበጡ ምሁራን የዴሞክራሲ ትርጉም ግልፅ አይደለም። በቃሉ ትርጉም መግባባት ሳይደረስ ” ዲሞክራሲ ያስፈልጋል /አያስፈልግም?…አለ ወይስ የለም? ” በሚለው እሰጣገባ ውስጥ የተገባበት አጋጣሚዎች አሉ። በዛ ላይ “ዲሞክራሲ” የሚለው ቃል እንደ ቃልኪዳን ቀለበት የስም ማስጌጫ ጣቱ ላይ ያላጠለቀ አለመገኘት ትርጓሜውን አደናጋሪ ያደርገዋል። እስቲ ይታያችሁ ባለፋት ሁለት ወራት ከ150 በላይ ኢትዬጲያውያንን በጠራራ ፀሐይ የገደለው ህውሀት የለበሰው ” ኢሕአዴግ” የሚባል ጭምብል በውስጡ “ዲሞክራሲ” የሚል ቃል አለው።
ስለዚህ እንደ አትሌት ሐይሌ ያሉ ሰዎች በትርጉም እና አስፈላጊነት ላይ ተደናግረው ብንመለከት ሊገርመን አይገባም። አብዛኛውን ጊዜ እነ ሐይሌ አዲስ እውቀት የሚጨምሩት በቃላት ትርጉም ላይ ልሂቃን እና ድርጅቶች ተስማምተው ተመሳሳይ ንግግር ሲናገሩ ካዳመጡ ብቻ ነው። ድፍረት ባይሆንብኝ የእነ ሐይሌ የእውቀት መጨበጫ ስልቱ በአይን የሚታይ የተግባር እንቅስቃሴ እንጂ በንባብ እና ምርመራ የሚገኝ አይደለም ።
በንባብ የሚገኝ ቢሆንማ ኖሮ አንጋፋው ፕሮፌሰር መስፍን ” ዴሞክራሲ ወይም ስልጣነ ሕዝብ ምንድነው? ” በሚለው ፅሁፋቸው ያሰፈሩትን በመመልከት ብቻ ግንዛቤ መጨበጥ በተቻለ ነበር። ፕሮፌሰር እንዲህ ይላሉ ፣
” ዴሞክራሲ ማለት የስልጣን ባለቤት ሕዝብ የሆነበት ስርአት ማለት ነው። መነሻው እና መድረሻው ይህ የህዝብ የሥልጣን ባለቤትነት ነው። የሥልጣን ኮርቻው ላይ መውጣትም ሆነ ከዚያ ኮርቻ ላይ መውረድ የሚቻለው በሕዝብ ፍቃድ ብቻ ነው” በማለት ይገልፁታል።
ፕሮፌሰሩ የዲሞክራሲን ትርጉም ብቻ አልሰጡንም። ዲሞክራሲን በራሳቸው መነጵር ሲመለከቱት ምን እንደሚሰማቸው እንደሚከተለው ገልጸዋል ፣
” እኔ ዴሞክራሲን የማየው ምንግዜም ደማቅ ብርሐን ያለበት ለጥ ያለ ሜዳ ላይ እንደተንጣለለና መጨረሻው እንደማይታይ ጥሩ የአስፋልት መንገድ ነው። ቁም ነገሩ እዚያ መንገድ ውስጥ መግባቱ ነው። ብርሃኑ ማንኛውንም ነገር አጋልጦ የሚያሳይ ሲሆን ለጥ ያለው የአስፓልት መንገድ ደግሞ እንደልብ የሚያስጋልብ ነው።”
2• የኢትዬጲያ ችግር ማጠንጠኛ ” የዲሞክራሲ እጦት” መሆኑን ያለመረዳት
ዛሬ አገራችን ኢትዬጲያ የምትገኝበት ሁኔታ ከመቼውም በባሰ አስቸጋሪ ሆኗል። በተለይም ባለፏት ሩብ ምዕተ አመት በኢትየጵያ ህዝብ ላይ ተንሰራፍቶ የተቀመጠው አገዛዝ ሀገራችን የመኖር እና ያለመኖር የህልውና ጥያቄ ውስጥ እንድትገባ አድርጓል። ስርአቱ በዚህ መልኩ ከቀጠለ እና ስር ነቀል ለውጥ ካልመጣ ይቺ በነጥቆ በራሪ ( roving bandits) የተወረወረች ምስኪን ሀገር ወዴት ልታመራ እንደምትችል መገመት አያዳግትም።
ከአንድ ሳምንት በፊት የአርበኞች ግንቦት ሰባት ሊ/መንበር በአሜሪካ ሀገር ሜሪላንድ ግዛት ለህዝብ ንግግር ሲያደርግ ተገኝቼ ነበር። ፕሮፌሰር ብርሃኑ ባደረገው ንግግር ሀገራችን የገባችበት አዘቅት መሰረታዊ ምንጩ ” ዲሞክራሲያዊ ስርአት” ባለመኖሩ እንደሆነ በቀይ ብእር አስምሮበታል። የሕዝብ ከመኖሪያው መፈናቀል፣ የህዝቡ በስርአቱ መማረር፣ የመንግስት በህዝብ ተቀባይነት ማጣት፣ አድሎአዊ የሆነ ስርአት መስፈን፣ የወጣቶች ስደት፣ ረሐብ እና የኢኮኖሚ ድቀት መንስኤው የእውነተኛ ዲሞክራሲ አለመኖሮ መሆኑን አስረድቷል። የሟሸሸና ጭንጋፍ መንግሥት ባለበት ሁኔታ ዲሞክራሲ ሊመጣ እንደማይችል አስገንዝቧል ። በዚህ አባባል ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ ።
ርግጥም ፕሮፌሰሩ እንደተገለፀው በኢትየጵያ “እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ስርአት” እስካልመጣ ድረስ የህግ የበላይነት ሊሰፍን አይችልም። ፀረ ዲሞክራሲ ዙፋኑን በጨበጠበት ሁኔታ ሁሉም ዜጐች በኢትዬጲያዊነታቸው ብቻ በህግ ፊት እኩል የማይታዩበት ፣ የዜግነት መብታቸው በተግባር የማይረጋገጥበት ሁኔታ ይፈጠራል። ተፈጥሯልም።
ዛሬ በህዝቦች መካከል በታቀደ መልኩ ጥርጣሬ እና ጥላቻ እንዲሰፍን እየተደረገ ነው። የወጣቱ የወደፊት ተስፋ ጨልሞ ስደትን እንደ አማራጭ ወስዷል። በጥቂት የሞራል ድህነት እና የበታችነት ስሜት በተጠናወታቸው ጠባብ ዘረኞች ሀገራችን ወደ መቀመቅ እየተገፋች ነው። የዜጐች የመናገር፣ የመጳፍ፣ የመደራጀትና ሌሎች መሰረታዊ መብቶች የ50ኛ አመቱን ” Golden Jubuilee” እያከበረ ካለው የኢቲቪ መስኮት ውጭ ማየት አልተቻለም።
3• “ፓለቲካ ሳይንስም ጥበብም” መሆኑን ያለመገንዘብ
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የነበሩት ጆን ኦፍ ኬኔዲ በበርካታ ድንቅ ንግግራቸው ይታወቃሉ። በተለይም ” ፓለቲካ ጥበብ (አርት) እና ሙያ… ያውም የተከበረ ሙያ ነው” በማለት አጠንክረው መግለጳቸው በብዙዎች ይታወሳል። ታዲያ ይህን ባህርዩን የተከበረ ሙያ እና ላቅ ያለ ማህበራዊ ሳይንስ መሆኑን ባለማወቅ አንዳንድ እንደ ሐይሌ ያሉ ታላላቅ ሰዎች ” አዳፋ ቃላትን” ሲናገሩ ይደመጣል።
ክፋቱ ደግሞ የሚናገሩት ከሕዝብ ፊት ስለሆነ ከንፈራቸው ተከፍቶ ሳይዘጋ ጉዳቱ በራሳቸው ላይ ይደርሳል።
እናም አትሌት ሐይሌ ፓለቲካና የዲሞክራሲ ጵንሰ ሐሳብ መረዳት በማለዳ ተነስቶ ” 84 ኪሎ ሜትር ልሩጥ” እንደ ማለት የቂል ድፍረት አይደለም። የአገር እና ህዝብን ሁለንተናዊ ሕይወት የሚመለከት እንደ አገር የመቀጠልና ያለመቀጠል የህልውና ጥያቄ ነው። የእውነተኛ ዲሞክራሲ መስፈን እና ያለመስፈን ጥያቄ በአሁን ሰአት ኢትዮጵያ የገባችበትን ቀውስ የመሻገር አሊያም ላታንሰራራ የመውደቅ ነው!!

Mittwoch, 10. Februar 2016

ማንነት በመሬት ላይ አይዘራም - ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ

ማንነት በመሬት ላይ አይዘራም - ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ

ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ማንነት ዋና የመወያያ ርእስ ሆኖ ቈይቷል። የሥነ ልቡና ምሁራን identity crisis የሚሉት ነው እንዳልል ያተኰረው “እኔ ማነኝ” ከሚለው ላይ አይደለም። ያተኮረው “ማንነት ከመሬት ጋር ይያያዛል ወይስ አይያያዝም?” ከሚለው ጥያቄ ላይ ነው። ውይይቱን እንዳዳመጥኩትና እንደሰማሁት፥ እኔም አስተያየቴን እንድሰጥ ተጠይቄ እንደተቸሁት፥ ማንነትን ከመሬት ጋር የሚያያይዙ እምነታቸውን ከሃይማኖት እምነት ደረጃ አድርሰውታል። ስለዚህ እነሱን በማስረጃ ማሳመን ሃይማኖታችሁን ለውጡ እንደማለት ሆኗል። “እምነቱ አገር አጥፊ ነው፤ ተውት” ቢባሉም፥ ማንነታቸው ከያዙት መሬት ጋር ከተቆራኘ፥ ይህ አደገኛ አቋማቸው ለሚያስከትለው ሀገራዊ ችግር አንዳች ሥጋት አይታይባቸውም። ክልል ይዞ ኢትዮጵያዊ መሆን ይቻላል የሚሉም አይጠፉም። መሳሳታቸውን መስማት አይፈልጉም፤ ግን ማንነት የሚዘራበት መሬት የሚያስፈልገው ዳጉሳ አይደለም።

ይህ አቋም በተለየ በኦሮሞ ድርጅቶች ዘንድ በግላጭ የሚታይ ነው። ማንነትን ከመሬት ጋር የማያያዝ ጥያቄ የተነሣው የአዲስ አበባ መስፋፋት ገበሬዎቹን ከመሬታቸው ማፈናቀሉ ነው። (በነገራችን ላይ፥ “አማሮች የኦሮሞዎችን መሬት ነጥቀው ኦሮሞዎችን መሬት-አልባ አድርገዋቸዋል” ሲባል ቆይቶ፥ ድንገት ባለመሬት ሆነው የከተማ መስፋፋት ነጠቃቸው!)

በታሪክም ሆነ በአስተሳሰብ ማንነት ከመሬት ጋር ግንኙነት የሌለው የማኅበረ ሰብ ክሥተት። ማንነትን ከመሬት ጋር ማያያዝን የዲሞክራሲ አስተሳሰብ ነው ይሉናል። ግን እንኳን ዲሞክራሲ ሊሆን ከሰብአ ትካት አስተሳሰብ እንኳን ወደኋላ ርቆ መሄድ ነው። እስቲ የነገድን አጀማመርና እድገት እንመልከት። ነገድ፥ እንደ ነገደ እስራኤል፥ ከቤተሰብ ይጀምራል። እስራኤል የእስራኤላውያን አባቶች ስም ነው። ነገደ እስራኤል የሆኑት የሱ ልጆች ናቸው። በዚያን ጊዜ ቤተሰብ የሚኖረው እያደነና ወፍ-ዘራሽ ፍሬ እየለቀመ ስለነበረ፥ ኑሮው አደንና ፍሬ ወደሚገኝበት ቦታ እየተዘዋወረ እንጂ ለማንነቱ ሲል አንድ ቦታ ኖሮ አልነበረም። ይህ የተፈጥሮ ክሥተት ዛሬም በዱር አራዊትና በወፎች በአንበጣዎች ላይ ይታያል። ማንነታቸው የተመሠረተው አብሮነታቸው ላይ ነው እንጂ በሚያርፉበት መሬት ላይ አይደለም። የሚያርፉበትን መሬትማ ከበሉት በኋላ ወደሌላው ይሄዳሉ። አገር መያዝ የተጀመረው ሕዝብ እየበዛ ስለሄደና አደን ላይ ግጭት ስለተፈጠረ ነው። አንድ ሕዝብ አገሩ ያልሆነውን አገሬ ነው ካለ መሬትና ማንነት ያልተያያዙ መሆናቸውን መመስከሩ ነው።

ኢትዮጵያን እንኳ የምንፈልጋት አባቶቻችን ያወረሱን እናት ሀገራⶭን ስለሆነችና ስላደግንባት እንጂ፥ ማንነታችንን እንድንገልጽባት አይደለም። አንድ ኢትዮጵያዊ ማንነቱን ለመጠበቅ ከፈለገ፥ የሚያስፈልገው ኅብረተሰብ እንጂ፥ ኢትዮጵያ ውስጥ መኖር አይደለም። አሜሪካን አገር በኦሮሞነት እየኖሩ፥ “ለማንነቴ ኦሮማዊ መሬት ያስፈልገኛል” ማለት የአስተሳሰብ መዛባት ወይም ራሱን የቻለ የኦሮሞ አገር ለመፍጠር አቋራጭ መንገድ መያዝ ነው። አንድ ሕዝብ ከትልቁ አካል ተለይቶ ሌላ ሕዝብ ከሆነና፥ የራሱን መሬት ከያዘ በኋላ፥ ተመልሶ የዚያ ሀገር ሕዝብ አካል መሆን የትም ሀገር አልታየም። ወያኔዎች የጎሳ ፖለቲካ ያመጡብን አናሳ ነገድ ስለሆንን ሁል ጊዜ ተገዢዎች ሆነን እንቀራለን ብለው በመፍራት ነው። በነሱ አስተሳሰብ እንኳን ብንሄድ ከሁሉ አስቀድሞ የሚቃወሟቸው ኦሮሞዎች መሆን ነበረባቸው።

አንዳንድ ኦሮሞዎች ይኸንን ጽሑፍ ሲያነቡ፥ “ማንነታችንን መግለጫ መሬት ይሰጠን ማለት ኢትዮጵያዊነታችን መካዳችን አይደለም” ሊሉ ይችላሉ። አወቁትም አላወቁትም ኢትዮጵያዊነታቸውን መካዳቸው ነው። በቅን መንገድ እንኳን ብናየው ሁለት ዜግነት መያዝ ነው። ሁለት ዜግነት የሚያዘው ደግሞ የሁለት ነፃ ሀገሮች ዜጋ ከሆኑ በኋላ ነው። ይኸንን ነው የምትፈልጉት? እንዲያውም “ስለኦሮሞ ገበሬ ርስት መነጠቅ ስንጋደል ዝም ብላችሁ ታዩ ነበር” ሲሉ ተሰምተዋል። የኦሮሞዎች ነገር ባንድ ራስ ሰባት መላስ ሆነብን። ድርጅቶቹ ብዙዎች ናቸው፤ ስለኢትዮጵያ ያለቸው አስተያየትም በዚያው ልክ ብዙ ነው። የቱን እንመን? የቱንስ እንቀበል? ከኦሮሞ ክልል ያባረሯቸውን አማሮች “ኑ ለኛ ጉዳይ ከኛ ጋር ተሰለፉ” ማለት ፌዝ አይሆንም? የኢትዮጵያን ባንዲራ ለማውለብለብ የተጸየፉ ኦሮሞዎች አማሮችን “ከእኛ ጋራ የኦሮሞን ባንዲራ አጅባችሁ አልተሰለፋችሁም” የሚል ወቀሳን የሚቀበል የኦሮሞ ፖለቲከኞች አእምሮ ብቻ ነው። የትኛውን የአማራ የፖለቲካ ድርጅት ነው ደግፈን የሚሉት? አማራው ጎሳ ላይ በተመሠረተ የፖለቲካ ፓርቲ ስለማያምን አልደገፍክም ተብሎ የሚወቀስ እንኳን ሰባት አንድም ድርጅ የለውም። ወቀሳው ሞረሽ ወገኔን ከሆነ፥ ይህ ድርጅት የተቋቋመው ኦሮሞዎች ሀብታቸውን ዘርፈው፥ ቤታቸውን አቃጥለው ያፈናቀሏቸውን አማሮች ለመርዳት የተቋቋመ የበጎ አድራጎች ድርጅት ነው። ወቀሳው ግለሰብ አማሮችን ከሆነ፥ ይኸው ኢትዮጵያዊ ሀብቱ መዘረፍ የለበትም እያልን እየጮህን ነው።

ሀገር የሕዝቧ እናት ነች። ሀገር በእናት የምትመሰለው፥ ልጆቿ ሁሉ እኩል እናቴ እንዲሏትና እኩል አንድታሳድጋቸው ነው። የእናት ሆድ ዝንጉርጉር ነው እንደሚባለው፥ ኢትዮጵያ የተለያዩ ልጆች ወልዳለች። በዝንጉርጉር ልጆቿ ማህል አለመግባባት አይፈጠርም አይባልም፤ ይፈጠራል። ግን ካልጠፋ መፍትሔ (ምርቷን እኩል እንካፈል ማለት እያለ) ምን ዓይነት አለመግባባት ነው እናታችንን እንቀራመት የሚል መፍትሔ የሚያስፈልገው? መሬቱን መካለል እናት ሀገርን መቀራመት መሆኑን የማያምኑ ሊኖሩ ይችላሉ። እርግጥ ካሉ ሞኞች ናቸው፤ ወይም “ክልሉ አገራችሁ አይደለም” እየተባሉ የሚገደሉትን፥ የሚባረሩትን፥ የሚዘረፉትን የሺዎች ሥቃይ እንዳይሰሙ ጆሯቸውን የዘጉ፥ እንዳያዩ ዓይናቸውን የጨፈኑ ይሆናሉ።

ግን በምን ምክንያት ነው ይኸ መፍትሔ በተለየ በትግሬና በኦሮሞ ፖለቲከኞች ዘንድ የተወደደው፤ በሌሎች ዘንድ የተጠላው?

የክልል ፖለቲካ አራማጆች የሚሰጡት ምክንያት “አማሮች ጨቁነውናል፤ ርስታችንን ወስደውብናል፤ ባህላቸውን ጭነውብናል። ይኸንን ሁሉ ተጽዕኖ ከጫንቃችን ልናራግፍ የምንችለው የራሳችንን አገር ስንገዛ ነው” የሚል ነው። ይህን አስተሳሰብ ቢመረምሩት ልክ ለማፍረስ እንዲመች ሆኖ የተቀነባበረ ደካማ አስተሳሰብ ሆኖ ይገኛል። እስቲ አንድ በአንድ እንየው፤ ያልተያዘ የኢትዮጵያ ክልል ከየት ይመጣል? ወይስ ሌሎች ኢትዮጵያውያን የያዙትን አገር የማስለቀቅ ወንጀልን ከመጨረሻው ለማድረስ ክልሉን ከሌላ ጎሳ ለመጽዳት ነው? በዚህ ቦታ ላይ የጥንቶች (አናሳ ጎሳዎች)፥ ከትናንት ወዲያ የመጡ (ኦሮሞዎች)፥ ትናንት የመጡ (አማራዎች፥ ትግሬዎች፥ ወዘተ) ሰፍረውበታል። ኦሮሞዎች ይኸንን ቦታ የኛ የግል ግዛት ይሁን የሚሉት በየትኛው የተለየ መብት ነው? ማንነትን ከመሬት ጋር ካያያዙት፥ እንግዛው በሚሉት ምድር ላይ ከኦሮሞ ወረራ በፊት የነበሩ ኢትዮጵያውያን ማንነት እንዴት ሊሆን ነው? ወይስ እነሱ የጠሉትን የባህል ጭቆና ከሌሎቹ ላይ ለመጣል ነው?

“የማንን ርስት ማን ወሰደው” የሚለውን ጥያቄ ታሪክ አስተካክሎ መልሶታል። በዚያ ምድር ላይ በዓሥራ ስድስተኛው ምእት ዓመት በረይቱማና ቦረን እስኪወሩት ድረስ አንዳች ኦሮሞ ዝር አላለበትም ነበር። አሁን አብዛኛው የኦሮሞዎች ርስት ሆኖ ሳለ፥ ርስታችንን አማራ ቀማን ማለት ጩኸቴን ቀሙኝ ይሆናል።

ያልተራገፈ ጭቆና የትኛው ነው?

ትልቁ ጥያቄ፥ “ክልል ካልያዙ ባህል ማዳበር አይቻልም” የሚለው ነው። ይኸም አሸዋ ላይ የቆመ እፍ ቢሉት የሚገረሰስ ጥያቄ ነው። ባህል ማዳበር ማለት ቋንቋን ማዳበር፥ ሙዚቃን፣ ሃይማኖትን መኮትኮት ነው። ለዚህ ጥረት መሬት ከልሎ መያዝ አያስፈልገውም። የሚያስፈልገው ሙያተኞች ነው። ለምሳሌ፥ አሜሪካ ሆኖ የአማርኛ መጻሕፍት ማሳተምና ለገባያ ማዋል፥ ሙዚቃ በኦዲዮ ማሰራጨት እንደሚቻል ብዙዎች አሳይተዋል። ኢሉባቦር ሆኖ ወለጋ ውስጥ የሚነበብ መጽሐፍ መጻፍ ይቻላል። ሁለቱ አውራጃዎች አንድ ክልል ውስጥ ካልገቡ አይቻልም የሚያስብል ምክንያት የለም። እስፓኛ የተጻፉ መጻሕፍት ዋና ገበያቸው ላቲን አሜሪካ ነች። እንግሊዝ አገር የሚጻፉ መጻሕፍት ገበያቸው አሜሪካ፥ ካናዳ፥ አውስትራሊያ፥ ኒው ዚላንድ ነው።

ከሁሉም የሚገርመው፥ “በክልል ተከፋፍሎ መኖርን አለመቀበል ወያኔዎች የፈጠሩትንና ሥር የሰደደውን የጎሳ ወይም የነገድ ፖለቲካ አለመቀበልና ወደኋላ መሄድ ነው” የሚለው ፈሊጥ ነው። ይኸ የ “የወያኔዎችን ከፋፍለህ ግዛው እቀፉ” ጥሪ ነው። የተላከውም በግላጭ ለአማሮች ነው። ጎሰኝነት ይሰማኝ ቢሆን ኖሮ ጥሪው ያኮራኝ ነበር። ምስጢሩ፥ “የጎሳን ፖለቲካ የሚቃወሙ፥ በዲሞክራሲ የሚያምኑ አማሮች ናቸው” ማለት ነው። አማሮች ጎሰኝነትን የሚቃወሙት፥ ጎሰኝነት የአንድን ሀገር ሕዝብ ስለሚለያይ፥ በጠላትነት ስለሚያፋጥጥ፥ ጎሰኝነትና ዲሞክራሲ የማይታረቁ ሥርዓቶች ስለሆኑ ነው። ንጉሣዊውን ሥርዓት ለመጣል የታገሉት የአማራ ልጆች የዲሞክራሲን ሥርዓት ለማስፈን ነበር። የደርግን ሥርዓት ለመገርሰስ ደማቸውን ያፈሰሱት የአማራ ልጆች የዲሞክራሲን ሥርዓት ለማስፈን ነበር። የአማራ ልጆች አሁንም የሚታገሉት የጥንቱን ዓላማቸውን አንግበው ነው። የአማራ ልጆች ኢትዮጵያ ነፃ ሳትወጣ፥ በሀገራቸው የዲሞክራሲ ሥርዓት ሳይሰፍን እንቅልፍ አይወስዳቸውም። ዲሞክራሲ የነፃና የሠለጠነ ሕዝብ አስተሳሰብ ስለ ሆነ፥ ኋላ ቀር በሆነው የጎሳ አስተሳሰብ አእምሯችሁ የታሰረባችሁ ኢትዮጵያውያን መታሰሪያችሁን በጣጥሳችሁ በዲሞክራሲ ትግል እንድተተባበሯቸው የአማራ ልጆች የአክብሮት ጥሪ ያቀርቡላችኋል።

በብዙ ትግል ኢትዮጵያን እንደገና ያገነኗት ጀግኖች ከሁሉ ነገድ የተውጣጡ የኢትዮጵያ ሕዝብ አባቶችና እናቶች ናቸው። የአንዱን ነገድ አስተዋጽዖ በጎም ሆነ ክፉ ማጋነንና የሌላውን ማቃለል በአብሮ መኖር አለማመን ነው።

http://wp.me/s5L3EG-633

Sonntag, 7. Februar 2016

ለመሆኑ የቀረች እንጥፍጣፊ ዕንባ አላችሁን? ነውስ አለቀባችሁ – ተለቃለቀ?

ከዕንባ ብዛት የተነሳ ዓይንም መሲና አንዲሆን ተፈረደበት … እህህ!  … እም!
ከሥርጉተ ሥላሴ 24.11.12
“ሰቆቃው ጴጥሮስ”
„አየ፣ ምነው እመ ብርሃን? ኢትዮጵያን ጨከንሽባት?
ምነው ቀኝሽን እረሳሻት?
እስከ መቼ ድረስ እንዲህ፣  መቀነትሽን ታጠብቂባት?
ልቦናሽን ታዞሪባት?
ፈተናዋን፣ ሰቀቀኗን፣ ጣሯን ይበቃል ሳትያት?
አላንቺ እኮ ማንም የላት …
አውሮፓ እንደሆን ትነጋዋን በፋሽስት ነቀርሳ
ታርሳ፣ ታምሳ፣ በስብሳ
ሂትለራዊ እባጭ ጫንቃዋን፣ እንደ ኮረብታ ተጭኗት፣
ቀና ብላ እውነት እንዳታይ፣ አንገቷን ቁልቅል ጠምዝዟት
ነፍሷን ድጦ ያስበረከካት
ሥልጡን ብኩን መፃጉዕ ናት፤ … „
እሳት ወይ አባባ – ከብላቴ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን መግቢያው ላይ  ከ 1ኛው እስከ 12ኛው ስንኝ ገጽ 131)
ዓይን ዕንባ ብቻ አይደለም ደምም … ያምጣል። እንዲህ ታሪክን  – ትውልድን አነጣጥሮና አቅዶ የሚገድል ዘመነ ጉዲት …. የሞቱትን ሳይቀር ከመቃብር አላስቀምጥ ብሎ በበቀል የሚያንገረግብ አማሽ ግበረ – አይሁድ ስታፈራ  ያቺ መከረኛ እናት ሀገር … ። ምን አላችሁ? ዓለም ዓቀፍ የታሪክ ጠበብትስ ከቶ ምን ይሉ ይሆን?!
አልበቃው አለ እኮ! ሀገር ምድሩ … ሜዳው መስኩ። ሁሉንም እንዳሻው ከተከተ – አፈለሰ። ይህም አላሰከነውም – የጤፍ ጠላውን። የበቀል ቀፈቱ አልሞላም። በሰማዕትነት ያለፉትንም ቋሳ የታጠቀው የህሊናው ባሩድ ወደ እነሱ አነጣጥሮ ትናንትን ነሰተ፤ በሰላም የረፉት ሳይቀር አላስተኛም አለ። አትንት ተቀጠቀጠጠ – ተፈጨ። እነሱንም አጽማቸውንም፤ ውዳሴያቸውንም- ድርሳናቸውንም  በፋስ ሊተረትር … ሊበታታትን … ። አዎን! ለጥፋት፤ ለድርመሳ ታጥቆ ተነሳ ወያኔ። ማህከነ! ዬሂትለር ግልባጭ ….
መሰረቱ ነው – የተፈጠረበት። መነሻው ነው – የተጠነሰሰበት። መዳረሻው ነው የተወለደበት …. ወያኔ ሲፈጠር ለማጥፋት ነው። ሲፈጠር ለመደምሰስ ነው። ሲፈጠር ለማፈረስ ነው። ታውቃላችሁን? ወያኔ ጫካ በነበረበት ጊዜ ያው የካቲት ላይ ዘመቻ ነበረው – የሚበላውን ለመስረቅ። ያን ጊዜ በጊዜያዊነት የሚይዛቸው ትናንሽ ከተሞች ወይንም ወረዳዎች ነበሩ። ታዲያላችሁ የደርግ ሰራዊት ሲያስለቅቅው … ት/ቤቶችን አፍርሶ፤ ድልድዮችን ንዶ፤ የውሃ ቧንቧዎችን ነቅሎ። ክሊነኮችን ባንኮች ዘርፎ ይሄዳል።
… ማለት እነዚህ ሁሉ የህዝብ የልማት ተቋማት ሆነው ወያኔ ግን የህዝብ ልማት አጥፊ የጎሳ ድርጅ ፤ የህዝብን ሁለገብ ጥቅም በቀጥታ ተጻራሪ በመሆኑ ካለምንም ርህራሄ ድብዛቸውን አጥፍቶ ይሄድ ነበር። እና አሁን … አሁን እኔ  „ ¡የልማት መንግስት¡“ እዬተባለ የሚደለቀው ቅራቅንቦ የወሬ ማሟያ  ተረት ተረት ከዛ በአካል ተገኝቼ ከአየሁት ተጨባጭ ሃቅ ጋር ሳንፃጽረው  የተሰነጠቀ ብርጭቆ ያደርገዋል።  ልማት እዬተባለ የሚደሰኮረውን ነገር …። ቀድሞ ነገር ወያኔ መገንባት ተፈጥሮው አይደለም። ለብዙኃኑ ኢትዮጵውያን መቆም ዕጣ ፈንተው አይደለም። ፍለጎ የፋቀው ነው። ካለ ተፍጥሮው ደግሞ ሊሆን የሚችል ከቶ አንዳችም ነገር የለም። በስተጀርባው የሚከውነው የፍልሰት ትዕይንት ካልኖረ በስተቀር … ወያኔ ወያኔ ነው። አራት ነጥብ በቀላለአጋኖ።!
ትክክለኛ የወያኔ ተፈጥሮ ማጥፋት ነው። አንድ ቀን የህዝብ ክሊንክ ቢዘጋ ስንት ሰው ይሞታል? ስንት ነፍሰጡር እናቶች ሊያልፉ ይችላሉ? ስነት ህጻነት ለጉዳት ይዳረጋሉ? የህን የሚያስተውልበት ህሊና ወያኔ አልነበረውም። አሁንም። በዚያን ጊዜ ለመሥራት ወይንም እንደ ገና ለመገንባት ደግሞ የሀገራችን አቅምን እሰቡት። … በተገለበጠ እውነት ተሸብሽቦ ነው እኮ ወያኔ ይህን ያህል 21 ዓመት ኧረ ለእኔስ እንደ 60 ዓመት የመከራና የሀዘን ዘመን ነው የምቆጥረው … በሦስት እጥፍ አባዙት … ወያኔ ሥልጣን ላይ የቆዬበትን …
ሲወድቅ እንኳን የሚኖርበን የቤት ሥራ ስታሰሉት … እንዴት እንዴት አድርጌ ልግለጸው  ይሆን? እንዲህ ይሻላል። … “ ከማህጸን ውስጥ ሲጠነሰስ ዓይኑ ያጣውን ዕንቡጥ ሲወለድ ዓይናማ ማደርግ ነው። „ ትውልዱን የሚጠብቀው የነጠረ ኃላፊነት። ከምን ዓይነት የብረት ቁርጥራጭ ብንሠራ ነው ይህን ትውልዳዊ ኃላፊነት በብቃት ተወጥተን ባለ አደረነታችን በተግባር የምናቀልመው … ?! እስከዚህ ድረስ ጥልቅ የፊት ለፊት የድርጊት የቤት ሥራ ዘመን ይጠብቃናል። ወያኔ ሲወድቅ እንኳን ዕዳው … እና የቆዬበት ዘመን በቀላል ስሌት 21 ዓመት ብቻ አይባልምና ነው … በሉ ስምምነት ላይ እንድረስ እሺ … የእኔ ክብሮች።
ሌላው ወያኔ የተፈጠረበትን ሚስጢር እሰቡት። ቁልጭ ያለ ነው። ጸረ ታሪክ ነው። አዎን ደፍረን እንናገረው። እራሱ ኢትዮጵያ የሚለው የወል መጠሪያ ቢለወጥ ደስታውን አይችለውም። ወያኔ  እኮ … ቱርኮች፤ ፖርቹጊዞች፤ ጣለያኖች፤ እንግሊዞች ቀብረውት ዬሄዱትን ፈንጅ ነው ጊዜ እዬጠበቀ እያፈነዳ ያለው …። አፄ ሚኒሊክና ኢትዮጵያን … አቡነ ጴጥሮስና እና ኢትዮጵያን እሰቧቸው። እንኝህ ቀደምት የሁሉም ነገር ዓርማችን፤ ሰንደቃችን፤ ማንነታችን፤ ታሪካችን፤ ትውፊታችን- አድህኗዊ እኛነታችን ናቸው።
አፄ ሚኒሊክ የኢትዮጵያ መሪ ብቻ አልነበሩም። የአፍሪካ መሪ ብቻ አይደሉም። የዓለም ጥቁሮች የነፃነት መሪ ናቸው። ከኒልሰን ማንዴላ በጣም እጅግ የቀደሙ።  የቅኝ ግዛትን ድህረ ፣ ማዕከለ፣ ቅድመ ራዕይ ከመሰረቱ ብትንትኑ የወጣው በአጤ ሚኒሊክ ነው። አጤ ሚኒሊክ አፍሪካን ሲቀረማት ለነበረው ኃይል ሁሉ የቀስተ ዳመና መቅሰፍት ናቸው። የቅኝ ግዛት አከርካሪን ብትንትኑን ያወጡ የጀግና ውጽፈተ ወርቅ ናቸው፤ የቅኝ ግዛት ዘመን እንዲያከትም ቅስሙን እንኩትኩት እንዲል ዓዋጅን በድል ያስጎሰሙ  ዬዓለም ዬጥቁሮች – ጥቁር አብነታዊ ምልክት – ዕንቁ ናቸው።  የ ሆ ን በ ት! የተፈለፈለ ድንቅነት የታተመበት። ኪናዊ የአርበኝነት ውሎ የተከተበበት። ፈዋሽ  – መድህን ዕሴት ናቸው አጤ ሚኒሊክ። ግርማቸው – ክብራቸው – እውነት አሁንም እዬት ይጣራል … በቃና!
„ዋ! … ያቺ ዓድዋ“
„ዋ!
ዓድዋ ሩቅዋ
የዓለት ምሰሶ አድመስ ጥግዋ
ሰማይ ጠቀስ ጭጋግ ዳስዋ
ዓድዋ ..
ባንቺ ብቻ ሕልውና
በትዝታሽ ብፅናና
በመስዋዕት ክንድሽ ዜና
አበው ታደሙ እንደ ገና …
ዋ!
ዓድዋ የዘር ዐፅመ ርስትዋ
የደም ትቢያ መቀነትዋ
በሞት ከባርነተ ሥርየት
በደም ለነፃነት ስለት
አበው የተሰውብሽ ለት፤
ዓድዋ
የኩሩ ትውልድ ቅርስዋ
የ ኢትዮጵያነተት ምስክርዋ
ዓድዋ
***
ዋ … ዓድዋ …
… ዓድዋ የትላንትናዋ
ይኽው ባንቺ ሕልውና
በትዝታሽ ብፅዕና
በመስዋዕት ክንድሽ ዝና
በነፃነት ቅርስሽ ዜና
አበው ተነሡ እንደ ጋና።
… ዋ … ያቺ አድዋ
ዓድዋ ሩቅዋ
የአለት ምሰሶ አድማስ ጥግዋ
ሰማይ ጠቀስ ጭጋግ  ዳስዋ
ዓድዋ … „
( እሳት ወይ አባባ ከብላቴ ሎሬት ጸጋዬ የግጥም መድብል ገጽ 56 ከሥንኝ 1 እስከ 19 በተጨማሪም ገጽ 58 ከ41 እስከ  52)
„ዋ! አድዋ“ ይህ ታሪክ ነው የኢትዮጵያን ተፈሪነትን ያመነጨው። የፈጠረው። ያፈለቀው። የደረሰው። የቃኘው። ይህ ለወያኔ ውጋቱ ነው። መጋኛው ነው። ስለዚህ ጊዜ ጠብቆ ወቅትን አጥንቶ በቀሉን ይፈጽማል። የወያኔ የ5 ዓመት በሉት የ10 ዓመት ዕቅድ ይኽው ነው የበቀል ዋንጫ …
ትንሽ ስለ ዕቅድ ልበል መሰል … መልክ እንዲኖረው አገላለጼ ..
  • የአጭር ጊዜ … ከቀናት እስከ አንድ ዓመት፤
  • የመካከለኛ ጊዜ ሊንክ ነው። ዬአጭር ጊዜውንና የረጅሙን ጊዜ የሚያይዝ፤
  • የረጅም ጊዜ ከ5 ዓመት ጀምሮ የሚኖሩትን ወቅታት … ንድፎችን ያካትታል …
በእነዚህ  የዕቅድ ጊዚያት ሁሉ  ወያኔ ሳይዘናጋ ቋሳም ቦታ አለው – ተመስጥሮ ይታቀዳል። አሁን ወያኔን በጣም የተዋጉት አካባቢዎች በሙሉ በወያኔ የሥልጣን ዘመናት ሁሉ አልተካተቱም። ናሙና …  ትሻላችሁን …. ? 21 ዓመት ሙሉ ጎንደር ውስጥ … ደብረታቦር … ጋይንት … አውራጃዎች እስከ ወረዳዎች ድረስ ተዘለዋል … ማለት ያው የአሽዋውና የስሚንቶ ድርድር ም ጸበለ ጻዲቅ አልደረሳቸውም ….
አንዲት የኢሰአት አድማጭ በቁጭት …. ከሐረር „የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ይባል የነበረው ት/ቤት ዛሬ ስሙ የለም ሲሉ“ አዳመጥኳቸው።  „ህዳሴ ግድበስ? ክፈለ – ከተማስ?“  ስም ጠፍቶ አይደለም  በአምሳላቸው የተሰዬሙት … ጥፋቱ መሰረት አለው። ጥፋቱ ዓላማ አለው። ጥፋቱ ታቅዶ ነው የሚከወነው።  ወ/ሮዋ  ከተገለጹት ውስጥ ደግሞ  … „አማራ መሆን ያሰፍራል ያስጠላል“ ብለዋል። አያስደንቅም። ወያኔ ለማጥፋትም የተፈጠረበት መሰረታዊ ዓላማ መቀመሚያው ይኽው ነው።
እንደ ወያኔ ውስጠ ተፍጥሮ ዕይታ … ዬኢትዮጵያ ታሪክ መሰረት አማራ ነው ብሎ ስለሚያምን – በቀዳሚ ጠላትነት ፈርጆታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖትም የአማራ ብቻ ነው ብሎ ስለሚያምን ለወያኔ በቀል ባለ ድርሻ ነው። አማርኛ ቋንቋ የአማራ ብቻ ነው ብሎ ስለሚያምን በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ዓይናማው የኢትዮጵውያን ወላዊ ድርሻውን የተወጣ ድንቅ ባለውለታ ጀግናም ባለ ቤለ ኃይሉ ታግሎታል፤
ወያኔ ያደገ ታሪክ በጅራፍ መገረፉ፤ በመዶሻ ዓናቱን መቀጥቀጡ፤ በሳንጃ ደረቱን መሰንጠቁን፤ በመጋዝ አንገቱን መቅላቱን፤ በሳንጃ ሽንጡን መከትከቱ፤ ከተፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ የሰራው የቤት ሥራው ነው። ከዚህ ጋር የተያያዙ የተሳሰሩ ሚስጢራዊ ነገሮች ደግሞ አሉ። የአማርኛ የሥነ  ጹሑፍ እድገት ደረጃ … ቅጥል ያደረገው፤ ያንገበገበው … አፍሪካዊው የቅኔው ልዑል ለዓለም አቀፉ ዬሎሬትነት ማዕረግነት የበቃው በአማርኛ ቅኔዊ ግጥሙ ነው። ይህም የቆሽታቸው ማላታይን ነው ለወያኔ። እኛ ብቻ አይደለም ጋሼ ጸጋዬን የምናከብረው … ሶኔትን – እንግሊዞች፤ ሌሪክን – ጀርመኖች፤ ሃይኩን – ጃፓኖች ሲፈጥሩ የኛው ሃብት ብላቴ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድህን ደግሞ 8ዬሽን ፈጠረ … ይህ አዲስ ዓለም ዓቅፍ ግኝት በመሆኑ ሰፊ ተቀባይነትና ተደማጭነትን በሥነ – ጹሑፉ ዓለም አስገኘ። እኛ ብቻ አይደለም ጋሼ ጸጋዬን  የምንወደው የምናከብረው፤ በእውነትም የምንሳሳለትም። …… ጀርመኖች፤ እንዲሁም ቀስተኞች ሲዊዞች ሳይቀሩ አፍሪካዊው ባለ ቅኔ ነው የሚሉት።
„ጨዋታን ጫዋታ ያነሰዋል“ ይላሉ ጎንደሬዎችና… እዚህ ላይ አንዲት ደስ የምትል መረጃ ላቀርብላችሁ ወያኔዎችም ይቀጠሉ … እዚህ እኔ ከምኖርበት ሀገር በ2012 ዓለም ዓቀፍ የፊደላት ቀን ይከበር ነበር። ከፍላዬሩ ላይ ፊደላችን ነበር። ስለ ፊደላችን ልዩ ታሪካዊ ተፈጥሮም መግለጫ ነበር። ይህም ብቻ አይደለም ከ18 ሀገር ቋንቋዎች ጋር አማርኛ ቋንቋ በድምጽ ሳይቀር ቦክስ ተሰጥቶት ለአንድ ወር የዘለቀ ኤግዚቢሽን ነበር። ከፈለጋችሁ ፍላዬሩን እልክላችኋለሁ። … ደስ አይልም? … እንዲያው ነጮቹ „አማርኛ ቋንቋን ግጥም ማደመጥ የምሽት ማህሌት እንደ ማደመጥ ነው። መንፈስን በልዩ ሁኔታ የሚገዛ ልዩ ቃናዊ መንፈስ አለው ይላሉ!“ እና ወያኔ እንዳሰበው ሁለመናዋን ማጥፋት፤ መሰረ ታሪኳን የሚናገሩ ቅርሶቿን ለማፍለስ ሆነ ለማክሰል  የፈለገወን ያህል ቢፍጨረጨርም አይችልም … ያበራል ገና ታሪኳ … ወያኔም ግን ይከስማል … እስነ ጉቱ … ድሪቶው … ከሥሩ …
መቼም እኔ በጣም ስጋት አለብኝ። 21 ዓመት አዲስ ትውልድ በቅሏልና። በትውልዱ ላይ እቦታው ተገኝቶ ለመሥራት ብዙ ነገሮች ስለሚያግዱ ይጨንቀኛል። አብዝቼ የምጨነቅበት ጉዳይ ነው። እግዚአብሄር ይመስገን የደራሲ አቶ ምስባህከ ወርቆ „ዴርቶ ጋዳ“ ጭብጥ መሰረት „ ሰቆቃው ጴጥሮስ ነው“ አሁን ደግሞ ቴዲዬ ዕፁብ ታሪክ ሠራ። አፄ ሚኒሊከን፤ እቴጌ ጣይቱን … ብላቴን በሥነ ጥበብ ተክሊል አጋባቸው። … ይህ ምን ያህል ሚሊዮን እንዳሰለፈ ያላችሁበት ነው። … እኔ እንኳን በሕይወቴ ሙዚቃ አዳምጬ አላውቅም። አሁን አደብ ገዝቼ አዳምጠዋለሁ። … ሶስት ሙሉው ሲዲ አለኝ። … ዝክረ ታሪክ ስለሆነ በዬቦታው ወዳጆቼ ላኩልኝ። ታዲያ ግን ነቀዙ ወያኔ ደግሞ ተርመጠመጠበት። ስለዚህ በብዙኃኑ ታዳሚ አፍቅሮት፤ አክብሮት ያገኘውን የታሪክ ወርቃማ ልቅ … በትኩሱ በማለት  …. እንሆ ታጥቆ ተነሳ – የአጤ ሚኒሊክም ሆነ  የሰማዕቱ የአቡነ ጴጥሮስም ሐውልት … ለማፍረስ …
የአጤ ሚኒሊክን ሀውልት ወያኔ መጀመሪያ እንደ ገባ  ዓይኑ ያረፈበት ጽኑ ጠላቱ … ነበር። ተንደርድሮ እንደገባ ገንባሌውን ሳይቀይር ያፈጠጠበት።  … የኦሮሞ ብሄረሰብ ወገኖቻችንም ከጥፋት ዓላማው ጋር ለማሰለፍ ብዙ የህሊና ሥራ ሰርቶበታል …።  እኔ እንጃ ሄሮድስም በዛች ግድም ዝር ሳይሉ እንደሆነ ነው አፈር የቀመሰቱ የሚመስለኝ … አንጡራ ጠላታቸው … ናቸውና ሁለቱም …።
ያው አባ ጳውሎስም ቢሆኑ … ሰማዕቱን ቅዱስ ጴጥሮስ ሲያዩ  በሸታቸው ይቀሰቀሳል …። የማህል ልባቸው ረመጥ ነበርና አይቅርብኝ እኔም ብለው ድቡሽታቸውን ከምረው አልፈዋል። ያው …  አንድ ቀን ዋጋውን ያገኛል። ወያኔንና የጥፋት ተልዕኮውን ምንም የዴሞክራሲ ቀመር ሳይታከክ ህዝብ ቀን የሰጠው ዕለት ብትንትኑን ያወጣዋል … ። ውሳኔ ህዝብንም አይጠብቅም። በዚያ ዕለት ህግ ጥሰት ነው።  … ወዮ! በሰላም ጊዜ እንዲህ እንዳሻህ ብሎ ትክሻውን ለማናቸውም ዓይነት የበቀል ክምር የደለደለ ትእግስት … የቆረጠ ዕለት።  ነገና እነሱን ያዬቸው ሰው …
እኔ እምሳበው ሆድ አደሩ ሁሉ ቁጭ ብሎ እራሱን ገዝቶ የሚመረምርበት ወቅት በራሱ ጊዜ- ጊዜ እዬሰጠው ነውና ከወያኔ ጋር መማዳሞዱን አቁሞ ከሚሊዮን ጋር ቢሰለፍ መልካም ነው። በስተቀር ግን „በሰፈሩት ቁና … „  …  እራሱ ወያኔ ከነ አካሉ ይፈርሳል። እንደ ቀደመው ጊዜ በሰው ሰውኛ አንሰበው … መንፈሳችነን  ከእዮር ጋር … ይሁን እሺ የእኔ ውዶች …  ባለቤቱ በትጋት አለና ለቤቱ ….
ይህ በራሱ መንፈሳችን በሃዲድ እርስ በእርሱ እንዲተሳሰር፤ በውል በኪዳን አንዲሰግር፤ ለስምረት በትጋት እንደንገሰግስ ኃይልና ጉልበት፤ ጥንካሬና ብርታት፤ መጽናነትና ፅናትን በስፋት የሚመግብ የህሊና ብቁ ስንቅ ነው። በደል ሲባዘ ይፈሳል። ሲከርም ይበጣሳል።
አንተ መዳህኒዓለም ዝምታህ በዛ! ቅጣቱን ቀጥል! አነባብር! እጅግ የናፈቀንን ንጹሕ አዬር እባክህን ለግሰን። ምን ሲሳንህ ሁሉ በእጅህ አይደለምን?!
እግዚአብሄር ይስጥልኝ።