Netsanet: የአይካ አዲስ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ሰራተኞች የስራ ማቆም አድማ መቱ

Dienstag, 3. Februar 2015

የአይካ አዲስ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ሰራተኞች የስራ ማቆም አድማ መቱ


በቱርክ ባለሃብቶች የተያዘው የአይካ አዲስ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ሰራተኞች ከጥር 23/2007 ዓ.ም ጀምረው የስራ ማቆም አድማ መምታታቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ኩባንያው በየ አመቱ በሚያደርገው የደመወዝ ጭማሬ መሰረት በዘንድሮው አመት የተሻለ የደመወዝ ጭማሬ እንደሚያደረግ የገለጸበትን ወረቀት ለሰራተኞቹ በትኖ የነበር ቢሆንም ቅዳሜ ጥር 23/2007 ዓ.ም ለሰራተኞቹ በተበተነው ሌላ ወረቀት የደመወዝ ጭማሬው ከተጠበቀው በታች ሆኖ በመገኘቱ ሰራተኞች ‹‹ስራ አንሰራም›› ብለው ፋብሪካው ግቢ ውስጥ ተቀምጠው ተቃውሟቸውን መግለጻቸውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ከሰኞ 25/2007 ዓ.ም ጀምሮ ኢትዮጵያውያን የድርጅቱ ሰራተኞች አድማውን አጠናክረው እንደቀጠሉ ታውቋል፡፡
ቅዳሜ ጥር 23/2007 ዓ.ም ሰራተኞቹ የደመወዝ ጭማሬውን ከሰሙ በኋላ ‹‹ስራ አንሰራም›› በማለታቸው የፋብሪካው ኃላፊዎች ‹‹የአንድ ወር ገደብ ስጡንንና እናስተካክል›› የሚል ጥያቄ ቢያቀርቡም ሰራተኞቹ በበኩላቸው ‹‹በሳምንት ጊዜ ውስጥ ይስተካከል›› የሚል ሀሳብ አቅርበው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሆኖም በሁለቱ መካከል ስምምነት ላይ መድረስ አልተቻለም፡፡ የመስሪያ ቤቱ ኃላፊዎች ሰራተኞቹን እየነጠሉ ለማናገር ያደረጉት ሙከራም እንዳልተሳካላቸው ተገልጾአል፡፡
ቅዳሜ ጥር 23 ዓ.ም ዝቅተኛ ነው የተባለው የደመወዝ ጭማሬ ምክንያት ስራ ሳይገቡ መስሪያ ቤቱ ግቢ ውስጥ ተሰብስበው የዋሉት የአይካ አዲስ ሰራተኞች ከትናንት ሰኞ ጥር 25/2007 ዓ.ም ጀምሮ የስራ ማቆም አድማ መምታታውን ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
አይካ አዲስ ከ8 ሺህ በላይ ሰራተኞች እንዳሉት የገለጸችው አንዲት የድርጅቱ ሰራተኛ ድርጅቱ ተመሳሳይ ስራ ላይ በተሰማሩ ኢትዮጵያውያንና የውጭ ዜጎች መካከል ደመወዝን ጨምሮ ከፍተኛ ልዩነት እንዳለና በኢትዮጵያውያን ላይ መድሎ እንደሚፈጽም ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጻለች፡፡ ከዚህ በደል በተጨማሪ ፋብሪካው የገባውን ቃል አለመፈፀሙ ሰራተኞቹ ስራ እንዲያቆሙ ምክንያት እንደሆነም ሰራተኞቹ ገልጸዋል፡፡

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen