Netsanet: የግንቦት 7 በአለም ዙሪያ የሚያካሄዳችቸዉን ህዝባዊ ስብሰባዎች ቅድመ ዝግጅት አጠናቀቀ

Dienstag, 2. September 2014

የግንቦት 7 በአለም ዙሪያ የሚያካሄዳችቸዉን ህዝባዊ ስብሰባዎች ቅድመ ዝግጅት አጠናቀቀ

Sep 1,2014
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በመላው ዓለም ከሚገኙ አባላት፣ ደጋፊዎቹና በአጠቃላይ ከኢትዮጵያውያን ጋር በወቅታዊ አገራዊ ሁኔታዎች ላይ ለመመካከር በ 26 ታላላቅ ከተሞች ያሰናዳቸው ህዝባዊ ስብሰባዎች ቅድመ ዝግጅት በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን ከድርጅቱ የተላከልን መረጃ ያመለክታል። ህዝባዊ ስብሰባዎቹ በሁሉም የአለም አህጉራት እንደሚካሄዱ የገለጸው ግንቦት 7 በመጭው ረቡዕ ኦገስት 27. 2014 በላስቬጋስ ዩኤስ አሜሪካ ተጀምሮ በሴፕቴንበር 14. 2014 በቤልጄም ብራስልስ በደመቀ ሁኔታ እንደሚጠናቀቅ ገልጿል።

በእነዚህ ታላላቅ ህዝባዊ ስብሰባዎች ላይ በጠላት እጅ ወድቀው የሚገኙት የንቅናቄው ዋና ፀሐፊ የአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ሥራዎች የሚወሱ ሲሆን ፋሽስቱ ወያኔን ማስወገድ በሚቻልባቸው ስልቶች ላይ ሰፊ ውይይት የድርጅቱ አመራሮች ከኢትዮጵያውያን ጋር እንደሚያደርጉ ተገልጿል። ትግላችን ሶስት የትግል ስልቶችን ያስተባበረ ነው ያለው የግንቦት 7 መልዕክት ሕዝባዊ ተቃውሞ፣ ሕዝባዊ እምቢተኝነት እና ሕዝባዊ አመጽ መሆናቸውን በመግለጽ እነዚህን ስልቶች በአገር ውስጥ እና ከአገር ውጭ በተቀናጀ ሁኔታ መተገበር በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ የድርጅቱ አመራሮች ከስብሰባው ታዳሚ ኢትዮጵያውያን ጋር ሰፊ ሰአት ወስደው ምክክር እንደሚያደርጉ ለማወቅ ተችሏል። ትግሉ አሁን ወሳኝ የትግል ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ የገለጸው ግንቦት 7 በተለይ በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ከድጋፍ ሰጪነት ወደ ተግባራዊ ተሳትፎ የተሸጋገሩበት ሁኔታን በመጥቀስ ለተቀሩት እስካሁን የትግሉ አካል ላልሆኑ ኢትዮጵያውያን ኑ! ኢትዮጵያ አገራችንን፣ ኢትዮጵያዊ ወገናችንን እና ራሳችን ነፃ ለማውጣት እና በሀገራችን ፍትህና ዲሞክራሲ እንዲሰፍን ለማድረግ በምናደርገው ትግል ተቀላቀሉን ሲል ጥሪ አቅርቧል። በሁሉም የህዝባዊው ስብሰባ ቦታዎች እስከዛሬ ድረስ ንቅናቄውን ለመቀላቀል የተቸገሩ ወገኖችን በትግሉ ለማሳተፍ ይቻል ዘንድ በአባልነትና ደጋፊነት የሚመዘገቡበት መድረክ መመቻቸቱንም ለማወቅ ተችሏል። በተጨማሪም በሁሉም ስብሰባዎች ላይ በረሃ የከተቱት የአርበኛ ወጣቶች ጥረት የሚዘከርበት መድረክ የተመቻቸ ሲሆን ለተቀሩት በአገር ውስጥና በውጭ አገር ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች፤ በሁሉም ደረጃ ለሚገኘው ኢትዮጵያዊ ሁሉ እና ለኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ጭምር የጉጅሌው ወያኔን አገዛዝ ለማስወገድ እየተደረገ ያለውን የሞት ሽረት ትግል እንዲቀላቀሉ ጥሪ እንደሚደረግ ለማወቅ ተችሏል።

ክቡራትና ክቡራን አድማጮቻችን የግንቦት 7 የፍትህ፤ የነፃነትና የዲሞክራሲን ንቅናቄ አለማቀፍ ህዝባዊ ስብሰባዎችን በተመለከተ ከየ አህጉራቱ የስብሰባው አዘጋጆችና አስተባባሪዎች ጋር ያደረግነውን ቃለምልልስ ማቅረብ የምንጀምር መሆኑን ለማሳሰብ እንወዳለን። በዚህ አጋጣሚ የሬዲዮ ክፍላችንም በየ አህጉራቱ ለሚገኙ ኢትዮጵያውያን በነዚህ ታሪካዊ ስብሰባዎች በመታደም እየተደረገ ስላለው የነፃነት ትግልና ስለደረሰበት ደረጃ ግንዛቤ እንዲወስዱ፤ በተመቻቸው መድረክ በመጠቀም ትግሉን በአባልነት ወይንም በደጋፊነት በመመዘገብ ድጋፍ እንዲያደርጉ መልዕክቷን ታስተላልፋለች።

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen