Netsanet: የአቶ ገብሩ አስራት መጽሐፍ ቅኝት – ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ (ሊያነቡት የሚገባ ትንታኔ)

Mittwoch, 17. September 2014

የአቶ ገብሩ አስራት መጽሐፍ ቅኝት – ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ (ሊያነቡት የሚገባ ትንታኔ)

በዋሽንግተን ዲስና አካባቢዋ ከሚታተመው ከዘኢትዮጵያ ጋዜጣ የተገኘ
Gebru Asrat
አቶ ገብሩ አስራት
ታሪክ የሚታወቀው ሲጻፍ ወይ ሲነገር ነው። መታመን አለመታመኑም የሚያከራክረው ተጽፎ ወይም በሌላ ቅርጹ ተመዝግቦ ሲገኝ ብቻ ነው። የታሪክ ታሪክነቱ ስነ ጽሑፉነቱ ሳይሆን ሁነቱ ክስተቱ በሆነ የጊዜ ገደብ ውስጥ መደረግ መፈጸሙ ነው። ካልሆነ ግን ልብወለድ ድርሰት መሆኑ አይቀርም። ሆነም ቀረ ግን ተፈጽሟል እንዲህ ሆኗል እንዲያ ነበር እያሉ ከነማረጋገጫው የሚነግሩን ታሪክ ዘጋቢዎች አሉ። ለተአማኒነቱ ሲባል ከስሜታዊ ወገንተኝነቱ እንዲጸዳ ታሪክ በታሪክ ሠሪዎች ባይጻፍም፣ እነሱ የሚተዉት ማስታወሻ ግን ለታሪክ ፀሐፊዎች ግሩም ስጦታ መሆኑ የታመነ ነው። አቶ ገብሩ አስራት በዚህ ረገድ ለታሪክ ፀሐፊዎች አንድ ማስታወሻ ትተዋል። መጽሐፉ ሰፕቴምበር 1/2014 በዋሽግንተን ዲሲ በተደረገ አንድ ሥነ ሥርዓት ተመርቋል። ዶ/ር ካሳ አያሌው በመሩት በዚህ የመጽሀፍ ምርቃት ፕሮግራም ላይ ተገኝተው መጽሐፉን የቃኙት አቶ ፈቃደ ሸዋቀናም መጽሐፉ ለሌሎች ፀሐፊዎች፣ ተመራማሪዎች፣ ፓለቲከኞችና አንባቢዎች እርሾ ሊሆን የሚችል ፈር ቀዳጅና አከራካሪ መጽሐፍ ሆኖ አግኝቸዋለሁ” ብለዋል።
እንደተባለውም ማከራከሩ አይቀርምና ታሪክ ፀሐፊዎች ወደፊት ፍሬውን ከገለባ ለይተው እውነቱን ከሐሰት አበራይተው ይህን ያለንበትን ዘመን ይገልጹታል። የታሪክ ማስታወሻ መተው እየተበራከተ ባለበት በዚህ ዘመን ዘመኑን አሳምሮና ወክሎ የሚገልጸው ታሪክ የትኛው እንደሆነ ማወቁ ይቸግረን ይሆናል።
ቢሆንም ነገሮች በፍጥነት መደበላለቅ በያዙበት በዚህ ዘመን የተደበላለቀ ስሜት የሚፈጥረው የአቶ ገብሩ መጽሐፍ ለታሪክ የሚተወው ማስታወሻ ምን ሊሆን እንደሚችል መቃኘቱ አይከፋም። ዘመኑን ያልተረጋጋ፣ የአፈና፣ የስደት፣ የመከፋፈል፣ የመከራ፣ የእስርና የጭቆና በማድረግ ግንባር ቀደም ተዋናይ ከሆኑት ሰዎች መካከል እግዜር አንዳንዱን እየመዘዘ ቶሎ ሳይዘነጉት፣ እያደረጉ ያሉትን ነገር ቆም ብለው አስተውለው እንዲጽፉት ሲያደርግ ደስ ያሰኛል። አቶ ገብሩም በመጽሀፋቸው ደጋግመው የሚጠቀሙባት “ አሁን ቆም ብዬ ሳዬው፣ አሁን መለስ ብዬ ሳየው፣ አሁን ሳጤነው” የምትል አገላለጽ አለች። ይክፋም ይልማም ቆም ብለው የሚቆጩበት ነገር አለ ማለት ነው። ለምሳሌ በመጽሀፋቸው ገጽ 249 ላይ “አሁን ሳጤነው በአብዮታዊ ዴሞክራሲ እምነታችን ምክንያት የመረጃ ፍሰትን ገድበን የአገራችንን የአስተሳሰብ እድገት በመጎተታችንና በማጫጨታችን እጸጸታለሁ።” ብለዋል።

ይህን ያጫጩትን የአስተሳሰብ እድገት ለማምጣት ከህሊናቸው ጋር ተማምለው ፋይዳ ያለው መጽሀፍ ለማዘጋጀት መነሳታቸውን በመግቢያቸው ጽፈዋል። “ ስለሆነም ለኀሊናዬ ትክክል የመሰለኝን ሁሉ ለማስፈር ሞክሬም፣ ሰማዕታቱ የተሰውለትን ዓላማ ለማክበር ሞክሬያለሁ” (ገጽ4) በማለት ከደጋፊዎቻቸውና ተቃዋሚዎቻቸው የሚመጣባቸውን ነቀፌታ የገመቱ መስለዋል። ሚዛናዊ ነኝና ልብ አድርጉልኝ ነው ነገሩ። ቢሆንም ነቀፌታውና ውርጅብኙን ያቆሙት ዘንድ ግን አይችሉም። የሚችሉትና ችለው ያሳዩት ነገር ለታሪክ የሚሆን ማስታወሻ መተው ነው። እሱን ትተውልናል! ጥያቄው የተውልን ነገር ምንድነው? የሚለው ነው። በዚህ ዘገባ “ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ” ከሚለው ባለ 516 ገጽ መጽሐፋቸው የተውልንን ማስታወሻ ከመጠነኛ አስተያየት ጋር መቃኘት ሞክረናል። መቸም የዘንድሮ መጽሐፍ ከድንጋይ ዳቦ ዘመን ካልጀመረ፣ ታሪክ ካላስተማረ አይሆንለትም። መጀመሪያ ረጀሙና ገናናው ታሪካችንን አንስተን እንጸልይበት ካለለ ወደ ፍሬ ነገሩ መምጣት ያስቀስፋል። ስለዚህ አንዴ ሺ ዘመን አንዴ መቶ ዓመት እየሆነ እንደ ስቶክ ማርኬት ገበያ የሚወጣ የሚወርደውን ዘመን እንለፈውና ወደ አቶ ገብሩ ዘመን ቀረብ ብሎ ያለውን የመጽሐፋቸውን ገጽ ገለጥ ገለጥ እናድርገው። መጽሐፉ በስድስት ም ዕራፎች በበርካታ ን ዑስ ም ዕራፎች የተከፋፈለ በቁመቱም ዘለግ ያለ ባለ 516 ገጽ ነው። አክሱምን የድርጅታቸውን የትጥቅ ትግል ዘመን ህወሓት ለሥልጣን የበቃበትንና ከኤርትራ ጋር በመንግሥት አብሮ የኖረበትን እንዲሁም ጦርነቱንን ከጦርነቱ በኋላ ያለውን ሁኔታ ሁሉ በዝርዝር ይዳ ስ ሳል። ሰለኢትዮጵያ የዴሞክራሲና ሰብ አዊ መብቶች አያያዝ ስለምርጫን የፖለቲካ ምህዳር መስፋት መጥበብ ያነሳል። መፍትሔ ሀሳቦች ናቸው የሚላቸውንም ሰንዝሯል። እጅግ የተደከመበት መጽሐፍ መሆኑ ያስታውቃል። ከመጽሐፉ ፍሬ ነገሮች ጥቂቶቹን ለመጋራት ያህል የሚከተለው ቅኝት ተደርጋል።

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen