Netsanet: (ሰበር ዜና) ለ1ዓመት ከ6 ወር በላይ በእስር ሲሰቃዩ የቆዩት 12 ተማሪዎች እና 1 መምህር የ6 ወር እስራት ተፈረደባቸው

Dienstag, 14. Oktober 2014

(ሰበር ዜና) ለ1ዓመት ከ6 ወር በላይ በእስር ሲሰቃዩ የቆዩት 12 ተማሪዎች እና 1 መምህር የ6 ወር እስራት ተፈረደባቸው

በእስር የቆዩበት ጊዜ ከተፈረደባቸው በመብለጡ ከእስር እንደሚፈቱ ተወስኗል!
ማክሰኞ ጥቅምት 4/2007
(ድምፃችን ይሰማ እንደዘገበው፡) ከ21 ወራት በፊት ከጅግጅጋ፣ ከሲቪል ሰርቪስ፣ ከባህር ዳር፣ ከጅማ፣ ከደሴ፣ ከሐዋሳና ከደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲዎች ታፍነው የታሰሩ 12 ሙስሊም ተማሪዎችና 1 አስተማሪ የስድስት ወር የእስር ቅጣት ተበየነባቸው! በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ወንጀል ሕግ አንቀጽ 32/1/ሀ፣ አንቀጽ 38/1፣ እንዲሁም አንቀጽ 257/ሀ ላይ በሰፈሩት አንቀጾች መሰረትነት የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ሃይማኖታዊ ስነስርአትና አለባበስን በሚመለከት ያወጣውን የስነምግባር ደንብ በመቃወም የተለያዩ አደረጃጀቶችን በመፍጠር ‹‹በመላው አገሪቱ አመጽ በመቀስቀስ በሃይማኖት ሽፋን በአገሪቱ ያለውን ሰላም ማወክ›› እና ‹‹የመፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎቹን በኃይል ለማስፈታት በመጣር›› የሚሉ ክሶች ተመስርተውባቸው ክሳቸው በልደታ ፍርድ ቤት ከ18 ወራት በላይ ሲታይ የዘለቀው ተማሪዎች ዛሬ የመጨረሻ ብይን በፍርድ ቤቱ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
(ሰበር ዜና) ለ1ዓመት ከ6 ወር በላይ በእስር ሲሰቃዩ የቆዩት 12 ተማሪዎች እና 1 መምህር የ6 ወር እስራት ተፈረደባቸው
መንግስት የበረታበትን የህብረተሰቡን ተቃውሞ ‹‹አስተነፍሳለሁ›› በሚል ዓላማ ከጥር 2005 ጀምሮ ከሚማሩባቸው የተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች አፍሶ ለእስር የዳረጋቸው እነዚሁ ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ መስከረም 27/2007 በፍርድ ቤቱ የጥፋተኝት ውሳኔ የተሰጠባቸው ሲሆን የቅጣት ብይን ለመስጠት ለዛሬ ቀጠሮ ያስቀመጠው ፍርድ ቤትም የስድስት ወራት እስርና ምክር እንዲሰጣቸው ወስኗል፡፡ በሃያዎቹ እድሜ መጀመሪያ ላይ የሚገኙት 13ቱ ተማሪዎች በመንግስት ኃይሎች ታፍነው ሲወሰዱ የዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን ለማጠናቀቅ ጥቂት ጊዜያት ብቻ ይቀራቸው ነበር፡፡
በእነ እስማኤል ኑርሑሴን መዝገብ የተከሰሱትና ብይን የተሰጠባቸው ተማሪዎች እስማኤል ኑር ሁሴን፣ ሰይድ ኢብራሂም፣ ሙሐመድ ሰይድ፣ ፈትሂያ ሙሐመድ፣ ኑርዬ ቃሲም፣ ያሲን ፈያሞ፣ መሃመድ አሚን፣ ዩሱፍ ከድር፣ ጣሂር መሃመድ፣ መሃመድ ሰይድ፣ አብደላ መሃመድ፣ አብዲ ሙሐመድ እና ኢብራሂም ዩሱፍ ናቸው። ከተከሳሾቹ መካከል ብቸኛዋ ሴት የህክምና ተማሪዋ ፈትህያም የክሱ ሰለባ ሆና በቃሊቲ እስር ያሳለፈች ሲሆን ከቤተሰቦቿ ጋር እንዳትገናኝም በወህኒው ሀላፊዎች እቀባ ተጥሎባት ይገኛል፡፡
በግንቦት 2005 ክስ የተመሰረተባቸው እነዚሁ ተማሪዎች በተለያዩ ሰበብ አስባቦች ምክንያት ችሎቱ እየተጓተተ በመቆየቱና የፍትህ ስርአቱ የዜጎችን መብት ማስከበር በማይችልበት ደረጃ በመኮላሸቱ ጥፋተኛ ሆነው ቢገኙ እንኳ ክሳቸው ከሚያስፈርድባቸው በላይ በእስር እየቆዩ መሆኑን የህግ ባለሙያዎች ሲያሳስቡ ቆይተዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ፍርድ ቤቱ ዛሬ የስድስት ወር ቅጣት ሲበይን ተማሪዎቹ በእስር ከ21 ወራት በላይ (ከተወሰነባቸው ቅጣት 3 እጥፍ በላይ) በቆዩበት ሁኔታ ላይ ነበር፡፡
እነዚህ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው በእምነታቸው ምክንያት ብቻ ከሌሎች ተማሪዎች ተነጥለው በድብደባ እና በተንዛዛ የፍርድ ቤት አሰራር መንገላታታቸው ሳያንስ የጥፋተኝነት ውሳኔ መተላለፉ አስደንጋጭም አሳዛኝም ነው፡፡ በተለይም ተማሪዎቹ ከትምህርት ገበታቸው ተፈናቅለው ሊመረቁ የሚችሉበት ጊዜ ያለፈ እና የቀሪዎቹም የተራዘመ ሲሆን አሁንም ቀጣይ የትምህርት እድላቸው ምን እንደሚሆን በውል አልታወቀም፡፡ በተማሪዎቹ ላይና በህዝቡ ላይ ለተዘነበለው ፍትህ የህግ ስርአቱ ተዋንያንና አጠቃላይ አስፈጻሚው አካል ተጠያቂ ሊሆኑ እንደሚገባ እሙን ቢሆንም የፍትህ ስርአቱ የመንግስት የፖለቲካ ማስፈጸሚያ ሸንጎ መሆኑ ሁሉንም ዜጋ ሊያሳስበው ይገባል፡፡
ህዝበ ሙስሊሙ እነዚህ ጀግና ተማሪዎች ይህን ሁሉ መስዋእትነት የከፈሉለትን ትግል ከዳር ለማድረስ ያለውን ቁርጠኝነት እየገለጸ ከዚህ ሁሉ ስቃይ በኋላም ቢሆን ተማሪዎቹ እንዲፈቱ ውሳኔ መሰጠቱ ለቤተሰቦቻቸው እና በዱዓና በጭንቀት ከጎናቸው ለቆመው ሁሉ መልካም ዜና መሆኑ አልቀረምና ለተማሪዎቹ እና ለቤተሰቦቻቸው ‹‹እንኳን ደስ አላችሁ!›› እያለ ይገኛል!
ትግላችን እስከድል ደጃፎች በአላህ ፈቃድ ይቀጥላል!
ድምፃችን ይሰማ!
አላሁ አክበር!

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen