Netsanet: አቡጊዳ – “ውድድር ጤናማ ጉዳይ ነው። መወዳደር አለብን (አንድነት እና ሰማያዊ) – የሰማይዊ አመራር አባል (ሰንድቅ)

Donnerstag, 17. April 2014

አቡጊዳ – “ውድድር ጤናማ ጉዳይ ነው። መወዳደር አለብን (አንድነት እና ሰማያዊ) – የሰማይዊ አመራር አባል (ሰንድቅ)

April 17/2014
የአንድነት ፓርቲ፣ ለሚያዚያ 26 ቀን በአዲስ አበባ ሰልፍ እንደጠራ፣ ከአዲስ አበባ አስተዳደሩ አስፈላጊዉን እውቅና እንደገኘ መዘገቡ ይታወቃል። በተመሳሳይ ሁኔተ የሰማይዊ ፓርቲ ደግሞ ከአንድ ሳምንት በፊት ሚያዚያ 19 ቀን በጃን ሜዳ ሰልፍ መጥራቱን ገልጿል። አስፈላጊዉን የማሳወቂያ ደብዳቤ ለአስተዳደሩ እንዳሰገቡ ሰማያዊቾ ቢገልጹም፣ በተባለው ቀን ከአስተዳደሩ እውቅና ይሰጣቸው አይሰጣቸው እስከ አሁን የተወቀ ነገር የለም።
ሰልፉን በጋራ መጥራት ለምን እንዳልተቻለ፣ ጉዳዩ የእሽቅድምድሞሽና ፖለቲካ ትርፍ ማግኛ እንደሆነና እንዳልሆነ መልስ ይሰጡ ዘንድ፣ የሰማያዊ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ሃላፊ አቶ ብርሃኑ ተክለ ያሬድ፣ በሰንደቅ ጋዜጣ ሲጠየቁ፣ እሽቅድምድሞሽ ባይባልም የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት እንደሆነ ግን ይናገራሉ።
በቃለ መጠይቃቸው ዉስጥ «አብረን ስለፍ ለማካሄድ ምንም ችግር የለም» ያሉት አቶ ብርሃኑ፣ ወረድ ብለው ደግሞ ሰማያዊ ከአንድነት ጋር እየተወዳደር እንዳለም ፣ ዉድድር ጥሩ እንደሆነም ሳይጠቁሙ አላለፉም።
ሰንደቅ ከአቶ ብርሃኑ ጋር ያደርገዉን ቃለ መጠይቅ የተወሰኑትን እንደሚከተለው አቅርበናል፡
ሰንደቅ፡- ከእናንተ ጋር በሚመሳሰል አጀንዳ አንድነት ፓርቲ አስቀድሞ ሰልፍ ጠርቷል። አጀንዳው ተመሳሳይ ከመሆኑ አንፃር ሰልፉን በጋራ ማካሄዱ አይሻልም?
አቶ ብርሃኑ፡- እንደተባለው አብሮ መስራቱ እንዳለ ሆኖ ያነሳናቸው ጥያቄዎች ምን ያህል ተመሳሳይ ናቸው? የሚለው ነገር በጣም ያሳስበናል። የእኛ ጥያቄ መንግስት ሀገር ማስተዳደር አልቻለም በሚል ነው የመብራት፣ የውሃና የስልክ ችግሮች እናንሳ እንጂ ከነዚህ ችግሮች ጋር ተያይዞ ፖለቲካዊ ጥያቄ ነው እያነሳን ያለነው። ሕዝቡ እየተቸገረ ያለው በኢህአዴግ የተሳሳተ ፖሊሲ ስለሆነ የእኛ ግልፅ የፖለቲካ ጥያቄ ነው።
ሰንደቅ፡- የአንድነት ጥያቄ ፖለቲካዊ የማይሆነው ከምን አንፃር ነው?
አቶ ብርሃኑ፡- በተደጋጋሚ ከአመራሮቻቸው እንደሚገለፀው፤ ጥያቄአቸው የፖለቲካ ሳይሆን የሕዝቡን ችግር ይዘን አደባባይ
መውጣት ስለፈለግን ነው ሲሉ እየሰማን ነው።
ሰንደቅ፡- እነሱም [አንድነት ፓርቲ] የውሃ፣ የመብራት፣ የስልክ መቆራረጥ በድምሩ ሲታዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች ጋር የተያያዙ እንደመሆናቸው መጠን ጥያቄው ፖለቲካዊ ነው ብሎ መፈረጅ አይቻልም? ምናልባት የእምነት ነፃነት የሰዎች መፈናቀልን ካለማካተታቸው ባለፈ በሌሎቹ ጥያቄዎች ላይ አብራችሁ መስራት አትችሉም ነበር?
አቶ ብርሃኑ፡- አብረን ሰልፉን ላለማካሄድ ምንም ችግር የለም። ዋናው እኛም ሰልፉን ለማካሄድ መግለጫ ስንሰጥ ማንኛውም የፖለቲካ፣ የሲቪል ተቋምና ሌሎች አብሮን እንዲሰራ ጠይቀናል፤ አብሮ መስራቱም ያለምንም ገደብ መሆኑን አስረድተናል።
ሰንደቅ፡- ቀድሞ ጥያቄ ያቀረበው አንድነት ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን ለብቻችሁ አዲስ ጥሪ ከማስተላለፍ አብሮ መስራቱ አይሻልም? አለበለዚያ በከተማዋ ውስጥ የሕዝብን ተቀባይነት ለማግኘት ጊዜአዊ የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት የሚደረግ
እሽቅድምድም እንደሆነም እየተገለፀ ነው::
አቶ ብርሃኑ፡- እሽቅድምድም አይደለም። የፖለቲካ ትርፍ ላልከው ግን ትክክል ነው፤ ለፖለቲካ ትርፍ ነው። ስራችንም ይሄው ነው። አጀንዳ እያነሳን ሕዝብ እያታገለን የሚፈለገውን መስዋዕትነት እየከፈልን ከዚህ ጎን ለጎን ፓርቲያችን ከሕዝብ ጎን የቆመ እንደመሆኑ አባላትን ለማብዛትና የተጠናከረ ስራ ለመስራት ጭምር ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ግን ጥያቄው የሕዝብ እንደመሆኑ መጠን እከሌ ቀድሟል እከሌ አልቀደመም የሚለው ሚዛን አይደፋም።
አንድነቶች ቢቀድሙንም የእምነት ነፃነት ጥያቄውና የሕዝብ መፈናቀሉ ሰለሚያሳስበን ከእነሱ የእኛ ጥያቄ ይሰፋል በተጨማሪም በመንግስትም ጫና ይሁን በእራሳቸው ችግር እስካሁን ሰልፉን ማካሄድ አልቻሉም።
ሰንደቅ፡- አንድነቶች ሰላማዊ ሰልፉን ላለማካሄዳቸው ማረጋገጫ አላችሁ?
አቶ ብርሃኑ፡- ማረጋገጥ የምንችለው በመጀመሪያ ደረጃ ሰልፉ ተጠርቶ የነበረው መጋቢት 28 ቀን 2006 ዓ.ም ነበር። የመጋቢት 28ቱ ውድቅ ከሆነ በኋላ ለሚያዚያ 5 ጠርተው ነበር፤ እንደገና ሚያዚያ 4 ተባለ። ስለዚህ ይህንን ጥያቄ እኛ
ይዘነው በተሻለ ዝግጅት ለመውጣት ነው ያሰብነው። ለዚህም ደግሞ በይፋ ጥሪ አድርገናል። በጋራ መስራት የሚቻል ከሆነም በጋራ እንስራው የሚል ውሳኔ ነው ያሳለፍነው።
ሰንደቅ፡- በዚህ ወቅት ሁለቱ ፓርቲዎች ጤናማ ግንኙነት አላቸው?
አቶ ብርሃኑ፡- እኔ በማየው ያለን ጤናማ ግንኙነት ነው ብዬ ነው የማምነው። አመራሮቻቸው ከአመራሮቻችን ጋር የጓደኝነት ግንኙነት አለን። ከዚህ የተለየ በተለያየ ፖለቲካ አጥር ውስጥ ያለን ሰዎች ነን። በተለይ በግል ጉዳይና በፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ጤናማ ግንኙነት አለን ብዬ አምናለሁ። አንዳንድ ግለሰቦች ጤናማ ያልሆነ ግንኙነት አለን ብለው ሊያምኑ ይችላሉ። በእርግጥም አንዳንድ ግለሰቦች ጋር ጤናማ የማይመስል ነገር ሊኖር ይችላል።
ሰንደቅ፡- በሰማያዊና በአንድነት ፓርቲዎች መካከል በአዲስ አበባ ውስጥ የፖለቲካ የበላይነት ለማግኘት ጤናማ ውድድር አለ ማለት ይቻላል?
አቶ ብርሃኑ፡- ውድድር ጤናማ ጉዳይ ነው። መወዳደር አለብን፤ ካልተወዳደርን ደግሞ አንድ መሆን ነው ያለብን። ሕዝቡ ውስጥ ተቀባይነት ለማግኘት ትክክለኛና የጠራ ትግል ማካሄድ አለብን። በእኛ በኩል በዚህ ትግል ውስጥ የሚያጋጥሙ መስዋዕትነቶች በልበ ሙሉነት የሕዝቡን ጥያቄ በማንሳት ማንኛውም ነገር ዋጋ እየከፈሉ በመሄድ ላይ ጠንካራ አቋም አለን።

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen