Netsanet: የኢትዮ ጂቡቲ ምድር ባቡር ዋና ሥራ አስኪያጅ በሙስና ተጠርጥረው በድሬዳዋ ከተማ ታሰሩ::

Donnerstag, 17. April 2014

የኢትዮ ጂቡቲ ምድር ባቡር ዋና ሥራ አስኪያጅ በሙስና ተጠርጥረው በድሬዳዋ ከተማ ታሰሩ::

April 16/2014

የኢትዮ ጂቡቲ ምድር ባቡርን ላለፉት በርካታ ዓመታት በዋና ሥራ አስኪያጅነት ሲመሩ የነበሩት አቶ ጥዑም ተኪዔ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ከሚያዝያ 2 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በድሬዳዋ ከተማ በእስር ላይ እንደሚገኙ ታወቀ፡፡ በሥራ ምክንያት ወደ ድሬዳዋ መሄዳቸው የተገለጸው አቶ ጥዑም፣ በተጠረጠሩበት የሙስና ወንጀል በቁጥጥር ሥር የዋሉት ባረፉበት ሆቴል መሆኑን የዓይን እማኞች ገልጸዋል፡፡
ለአቶ ጥዑም በቁጥጥር ሥር መዋል ዋናው ምክንያት በድሬዳዋ ከተማ የሚገኘው የኢትዮ ጂቡቲ ምድር ባቡር ስፖርተኞች (ሠራተኞች) ክበብ ጋር የተገናኘ ሳይሆን እንደማይቀር ምንጮቹ ተናግረዋል፡፡ ላለፉት ዓመታት ክበቡን በኮንትራት ይዘውት የነበሩ ግለሰብ የኮንትራት ጊዜያቸው በሰኔ ወር 2006 ዓ.ም. የሚያበቃ ስለሆነ፣ ኮንትራት እንዲያራዝሙላቸው ዋና ሥራ አስኪያጁን ሲለማመጡ እንደነበር ምንጮቹ ጠቁመዋል፡፡
አቶ ጥዑም ያረፉበት ሆቴል እንዲፈተሽ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ፀረ ሙስና መርማሪ ፖሊስ ከፍርድ ቤት ትዕዛዝ አውጥቶ ሲፈትሽ፣ ክበቡን በኮንትራት የያዙት ግለሰብ ለመርማሪ ፖሊሶች ያስመዘገቡት 2000 ብር በመገኘቱ፣ አቶ ጥዑም በቁጥጥር ሥር ሊውሉ መቻላቸውን አስረድተዋል፡፡ አቶ ጥዑም ሚያዝያ 5 ቀን 2,006 ዓ.ም. ድሬዳዋ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርበው ፖሊስ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ ጠይቆባቸው፣ በድጋሚ ሚያዝያ 7 ቀን 2006 ዓ.ም. መቅረባቸው ታውቋል፡፡ ፖሊስ ምርምራ እንደሚቀረው ለፍርድ ቤቱ በማስረዳት ተጨማሪ የ14 ቀናት ጊዜ ጠይቆ እንደተፈቀደለትና ለሚያዝያ 20 ቀን 2006 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱም ታውቋል፡፡ አቶ ጥዑም የተጠረጠሩበት ወንጀል ዋስትና የሚከለክል በመሆኑ የዋስትና መብታቸው መታለፉም ተገልጿል፡ሪፖርተር

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen