Netsanet: የኢትዮጵያ ሽግግር ምክር ቤቱ ኢፕሪል 13 ስብሰባን በተመለከተ

Dienstag, 8. April 2014

የኢትዮጵያ ሽግግር ምክር ቤቱ ኢፕሪል 13 ስብሰባን በተመለከተ


April 7/2014
የአንድነት ፓርቲ የሚሊዮኖች ንቅናቄ በሚል የጀመረው እንቅስቃሴ፣ በዉጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን ድጋፍ እያገኘ መጥቷል። ኢትዮጵያዉያን በአካባቢያቸው ካሉ የአንድነት ድጋፍ ማህበራት ጋር በመሆን ከሚደግፉት በተጨማሪ፣ የተለያዩ ሲቪክ ማህበራት፣ በዉጭ አገር ያሉ የፖለቲካ ደርጅቶች እንዲሁም ግለሰቦች ሳይቀር፣ ጉዳዩ የአንድ ፓርቲ ብቻ ሳይሆን የሕዝብ ጉዳይ ነው፣ በሚል ከሚሊዮኖች አንዱ ነን እያሉ ነው።ከነዚህ፣ አገር ቤት እየተደረገ ያለዉን እንቅስቃሴ ከሚደግፉ ድርጅቶች መካከል፣ የኢትዮጵያ ብሄራዊ የሽግግር ምክር ቤት አንዱ ነው። ምክር ቤቱ የራሱ አላማና ግብ ይዞ እየተንቀሳቀስ ያለ ደርጅት ነው።
በኢትዮጵያ የሚደረገዉን ሰላማዊና ሕጋዊ እንቅስቃሴ ምክር ቤቱ እንደሚደግፍ ብዙ ግዜ አሳዉቋል። አገር ቤት የሚደረገዉን ትግል የምክር ቤቱ መሪዎችና አባላት ያሳነሱበት፣ ያንቋሸሹበት፣ «አይሰራም፣ ጊዜ ማጥፋት ነው» በሚል በተዘዋዋሪ መንግስት ሕዝቡ ድጋፍ እንዳይሰጥ የሞከሩበት ጊዜ የለም። ይልቅስ ፣ የሽግግር ምክር ቤቱ፣ በዳያስፖራ ያለው የሚሊዮኖች ንቅናቄ ግብረ ኃይል ተወካዮችን ልኮ አብሮ የሚሰራ ከመሆኑም ባሻገር፣ በተለያዩ መግለጫዎቹ አገር ቤት ለሚደረገው ትግል ያለውን ሶሊዳሪቲ በገሃድ ያሳየ ድርጅት ነው።
ለምሳሌ ኦክቶብር ፣ 2013 የሽግግር ምክር ቤቱ «በኢትዮጵያ ዉስጥ የሚደረገዉን ትግል እንደግፋለን» በሚል ርእስ ያወጣዉን መግለጫ ማንበብ እንችላለን። መግለጫዉ «የኢትዮጵያ ብሄራዊ የሽግግር ምክር ቤት ለነዚህ ቆራጥ የፖለቲካ ድርጅቶች በተለይም ለሰማያዊ ፓርቲና የአንድነት ድርጅት አመራርና አባላቶች፤ እንዲሁም በየእስር ቤት ተወርውረው ለሚገኙት የኢትዮጵያ የክፉ ቀን ደራሽ ጀግኖች የድርጅት መሪዎችና ጋዜጠኞች፤ ያለንን ከፍተኛ አድናቆት ከመግለጽ ባሻገር፤ ይህንን ግፈኛ ስርአት በህዝባዊ አመጽ መታገልና ማስወገድ የድርጅታችን መርህ ከመሆኑ አኳያ ሙሉ ድጋፋችንን የምንሰጥ መሆኑን እናረጋግጣለን» ሲል ነው፣ አገር ቤት ላሉት ታጋዮች ምክር ቤቱ አጋርነቱን የገለጸው።
ምክር ቤቱ የአንድነት ፓርቲም ሆነ ሌሎች ሰላማዊ በሆነ መንገድ ታግለው፣ በምርጫ አሸንፈዉ፣ በሕጉ መሰረት ሕገ መንግስቱን አሻሽለው፣ ለሁሉም ዜጎች እኩል የሆነች፣ አንዲት፣ ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ ብትመጣ ፣ እንደ ማንኛዉም አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ የሚመኙትና የሚናፍቁት ነው። ለዚህም ነው ድጋፋቸዉን እየሰጡ ያሉት።
ነገር ግን ነገሮች እንደተጠበቁ ላይሄዱ ይችላሉ። «በአገራችን ኢትዮጵያ ያለው የፖለቲካ ቀዉስ የበለጠ እየከረረ፣ ኢሕአዴግ እርሱ ባወጣዉ ሕግ አልገዛም ብሎ፣ ሕገ ወጥና አምባገነናዊ እርምጃዎች በመዉሰድ ፣ ወደ አላስፈላጊ ደረጃ ከተኬደ፣ በኢትዮጵያ አናርኪ እንዳይፈጠር፣ ከወዲሁ አማራጭ መፍትሄ ማዘጋጀት ያስፈልጋል» ብለው በሽግግር ምክር ቤቱ የሚንቀሳቀሱ ወገኖች ያምናሉ። አሁን በስልጣን ላይ ያሉት አምባገነኖች ኢትዮጵያ እንድትፈራርስ ፍላጎት ሊኖራቸው ይችላል የሚል እምነት በመኖሩም፣ ከወዲሁ በተለይም በዉጭ ያለውን ኃይል በማሰባሰብና ወደ አንድ በማምጣት፣ ተጠባባቂ PLAN B ለማዘጋጃት እየሰሩ ነው። የኢትዮጵያ ብሄራዊ የሽግግር ምክር ቤት የሚል ስያሜም ለራሳቸው የሰጡት በዚህ ምክንያት ነው። ስልጣን ለመጨበጥ ሳይሆን፣ ነገሮችን በፈራረሱበት ወቅት፣ የሽግግር መንግስት ተቋቁሞ አገራችን እንደ አገር የምትቀጥልበትን ሁኔታ ለማረጋገጥ።
አገር ቤት ያለዉ ትግል ተጨባጭ ዉጤት አምጥቶ፣ በኢሕአዴግ እና በተቃዋሚዎች መካከል መግባባት ተፈጥሮ፣ አሁን ያለው ሕገ መንግስት ተሻሽሎ፣ ነገሮች ሁላችንም እንደምንፈልገው ቢሄዱና የሽግግር መንግስት ምክር አላስፈላጊ ከመሆኑ የተነሳ ቢከስም፣ ሁላችንም የምንመኘው ነው። ነገር ግን ያ እስኪሆን፣ «ምናልባት» በሚል መጠንቀቁ አስተዋይነት ነው። ለዚህም ነዉ ጥረታቸው ሊደገፍና ሊበረታታ የሚገባው።
የሽግግር ምክር ቤቱ፣ የፊታችን ሚያዚያ 5 ቀን በዋሺንግተን ዲሲ ስብሰባ ያደርጋል። ስብሰባዉን ላይቭ በፓልቶክ፣ ወይንም፣ ቴሌኮንፈራንስ የሚተላለፍ ከሆነ ለመከታተል እሞክራለሁ። በዲሲ አካባቢ ያሉ ኢትዮጵያዉያን በአካል ስብሰባዉን እንዲካፈሉ፣ ጥያቄዎችን እንዲጠይቁ፣ ሃሳባቸውን እንዲገልጹም አበረታታለሁ። በአገር ጉዳይ ላይ መመካከርና መወያየት ምንጊዜም ጠቃሚ ነውና።
ስብሰባው፣ ብዙ ጊዜ በዳያስፖራ ከተለመደውና አሰልቺ ከሆነው፣ አገዛዙን ከማዉግዝና ከመስደብ ፖለቲካ ያለፈ፣ የተጨበጡና ሥራ ላይ ያተኮሩ፣ ኢትዮጵያዊያን ማሰባብስ የሚችሉ፣ በሰለጠነ መንፈስ የሚቀርቡ፣ አንኳር ቁም ነገሮችን ጉዳዮችን አንስቶ እንደሚወያይ ተስፋ አደርጋለሁ።

Keine Kommentare:

Kommentar veröffentlichen